Thursday 27 November 2014

ተማሪዎች፣ መምህራን እና የተቋማት ፕሬዚዳንቶች ለአመጽ ተነሱ!


ዘረኛውና አምባገነኑ የህወሓት አገዛዝ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ከካድሬ ማሰልጠኛ ማዕከላትነት ለይቶ የማያይ ስለመሆኑ በተቋማቱ ውስጥ የሚደረጉ ተግባራት ማረጋገጫዎች ናቸው። ለዚህ ተግባሩ በሰነድ ደረጃ መቅረብ ከሚችሉት የቅርብ ጊዜ ማስረጃዎች ዋነኛው በህዳር 2007 ዓ.ም. በሥራ ላይ የዋለው “የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የኢህአዴግ የምርጫ ድል ልማት ሰራዊት ግንባታ አደረጃጀት ማንዋል” የተሰኘው በትምህርት ሚኒስቴር ተዘጋጅቶ ለሁሉም ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የተላለፈው ሰነድ ነው። ይህ ሰነድ፣ የህወሓት አሳፋሪ የትምህርት ፓሊሲ ባፈጠጠ መልኩ የተገለፀበት፤ የኢፌዴሪ መንግሥት ተብሎ በሚጠራው የህወሓት አገዛዝ ተቋም እና በህወሓት/ኢህአዴግ ፓርቲ መካከል ለይምሰል እንኳን ልዩነት አለመኖሩ በግላጭ የሚታይበት ሰነድ በመሆኑ በዚህ ርዕሰ አንቀሳችን በስፋት ልንዳስሰው ወስነናል።
ሰነዱ በትምህርት ሥርዓቱ ላይ መርዙን መርጨት የሚጀምረው ገና በመግቢያው ስለማንዋሉ አስፈላጊነት ሲገልጽ ነው። ማንዋሉ “ከምንም በላይየብጥብጥና የሁከት መንስኤ የሆነውን ተማሪ በኢህአዴግ አመራር አባላት እየታገዙ ለመያዝ የሚያስችል ነው” በማለት ህወሓት ተማሪውን የሚመለከተው “ከምንም በላይ በብጥብጥ መንስኤነት” መሆኑ፤ ለዚህ መድሀኒቱ ደግሞ ተማሪውን በኢህአዴግ አመራር አባላት “መያዝ” መሆኑን በማያሻማ ሁኔታ ይገልፃል። ቀጥሎም “በምርጫው ሊፈጠር የሚችለውን የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ሁከትና ብጥብጥ ለማስቆም በማደራጀት መረጃ ለመጥለፍ አመችነቱ የላቀ እንደሚሆን ታምኖበታል” በማለት መረጃ መጥለፍ የዩኒቨርስቲዎችና የትምህርት ሚኒስቴር ሥራ እንደሆነ አድርጎ ያቀርባል።
የማንዋሉን ዓላማዎች በሚገልፀው ክፍል ደግም “… የከፍተኛ ትምህርት የትምህርት የልማት ሰራዊት ግንባታን ወይም የፓለቲካ ሰራዊት ግንባታ በሁሉም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በተደራጀና በተናቀጀ ሁኔታ በማቀጣጠልና በማስቀጠል … ምርጫ 2007 ውጤታማ ለማድረግ እና የኢህአዴግን አሸናፊነት ለማረጋገጥ ነው” በማለት ተቋማቱን የኢህአዴግ የምርጫ መሣሪያ መሆናቸውን፤ ግባቸውም የኢህአዴግ አሸናፊነትን ማረጋገጥ መሆኑ ይገልፃል።
በገጽ 3 ላይ ደግሞ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች “በኢህአዴግ ላይ ያላቸው አቋም የወረደ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ በማንኛውም ተቃውሞ ድምፅ ከተጠሩ፤ ሰልፍ የሚያደምቁ፤ ተቃውሞን ከግብ ለማድረስ ሁነኛ መሳሪያ ናቸው። ተማሪዎች በየትኛውም ሐገር እንደታየው አደባባይን የመያዝ ህዝብን አስተባብረው ለተቃውሞ የማሳደም እድላቸው የሰፋ በመሆኑ ከዚህም ሲያልፍ፤ የኢህአዴግ ምከታን በመቃወም ለጠላት ጎራ ተሰልፈው የመታጠቅ እድላቸው ከፍተኛ ነው” ሲል “በወጣቱ እጠላለሁ” የሚለው የህወሓት/ኢህአዴግን ስጋት አፍረጥርጦ ያወጣል። ትንሽ ወረድ ብሎ ደግሞ “በተለይ በአሁኑ ሰዓት ፈተና ላይ የጣለን የምርጫ ጉዳይ እንደምናሸንፍ ቃል የተያዘለት ቢሆንም፤ ፈተናዎች የሚፈጠሩት በህዝብ እና በራሱ ታማኝ ባልሆኑ ሃይሎች ማለትም በመንግስት ክንፍ አይቀለበስም ብሎ ማሰብ አይቻልም። በዚህም ቀድሞ መዘጋጀት ያለበት እና ለሁከት እና ለብጥብጥ መሳሪያ ሊሆን የሚችለው የህዝብ ክንፍ የተማረው ሃይል ሊሆን ስለሚችል ሊታሰብበት ይገባል” ሲል በተማረው ወጣትና የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሠራተኞች ላይ ያለው ጥርጣሬና ፍርሃት ምን ያህል ከፍተኛ እንደሆነ ይገልፃል።
የ2007 ምርጫ በህወሓት ሹማምንት ላይ የፈጠረውን ጭንቀት በዚህ ሰነድ ላይ በገሀድ የሚታይ በመሆኑ እያንዳንዱ ዓረፍተ ነገር በጥንቃቄ ሊነበብና ሊተነተን የሚገባው ነው። ለምሳሌ በገጽ 6 ላይ ስለዩኒቨርስቲ ተማሪ ሲገልጽ “የአመፅ እና የብጥብጥ መነሻ ሊሆን የሚችል ሀይል መሆኑን በአክራሪዎች ሲጠለፍ፤ ከመንግስት ሃይማኖቱን እየመረጠ በባህር ዳር ዩኒቨርስቲ፤ በጅማ ዩኒቨርስቲ፤ በመቀሌ ዩኒቨርስቲ እና በሌሎችም ትምህርቱን ትቶ ሲኮበልል ተመልክተናል” ይላል። ለተማሪዎች፣ ከመንግሥት እና ከሃይማኖት አንዱን እንዲመርጡ ተደርጎ ሃይማኖታቸውን የመረጡ መኖራቸውን እና ይህ ደግሞ አደገኛ ነገር መሆኑን ነው ይህ ዓረፍተ ነገር የሚነግረን። ለመሆኑ ይህ ምን የሚሉት ምርጫ ነው? በእንዴት ያለ ሥርዓት ነው ዜጎች ከመንግስትና ከሃይማኖት አንዱን ምረጡ የሚባለው? እንዲህ ዓይነት ምርጫ ቀርቦ ሃይማኖትን መምረጥ እንዲህ ክፉ ነገር የሆነው ለምንድነው? ይህ ጉዳይ ብቻውን ብዙ የሚያነጋገር ነገር አለው።
በገጽ 8 ላይ ደግሞ “ከፍተኛ አመራሩ ተቋማዊ ለውጥ እንዲሁም የትምህርት ልማት ሰራዊት ግንባታ ቴክኒካዊ ሳይሆን ፓለቲካዊ ጉዳይ መሆኑን ተገንዝቦ ካለእርሱ ባለቤትነትና ቀጥተኛ ተሳትፎ ሰራዊት መገንባት እንደማይቻል በመገንዘብ የመሪነት ሚናውን ካለምንም ማወላዳት መወጣት ይጠበቅበታል” በማለት እየተሠራ ያለው የፓርቲ ወገንተኛ የሆነ ፓለቲካ መሆኑን ብቻ ሳይሆን የትምህርት ተቋማት መሪዎች ዋና ተልዕኮ ትምህርት ማስተማር ሳይሆን የወያኔ ፖለቲካን ማስፈጸም መሆኑን ምንም ሳይጎረብጠው ፍርጥርጡን ያወጣዋል። ትንሽ ወረድ ብሎም “የጋራ መግባባት የምንለካው በመጀመሪያ ለምርጫው የኢህአዴግ የድጋፍ የድል ሰራዊት ብዛት ነው” በማለት ከላይ ያለውን በማጠናከር ወገንተኛነቱም ለኢህአዴግ መሆኑ ያውጃል። በመጨረሻም “ … ሁሉም የዩኒቨርስቲ ፕሬዚዳንቶች ውጤታቸው የሚሞላላቸው ለምርጫው በሚያዘጋጁት የድጋፍ ሃይል ይወሰናል” በማለት የአካዳሚ ነፃነት ብቻ ሳይሆን የከፍተኛ ትምህርት ሥርዓትን ለቀብር ያዘጋጃል።
ይህ ነው የህወሓት የትምህርት ፓሊሲ! የዩኒቨስቲዎች ቁጥር ለማመን በሚቸግር መጠን ቢጨምር፤ የከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎች ቅበላ በብዙ መቶኛዎች ቢያድግ ጥቅሙ ምኑ ላይ ነው። በእንዲህ ዓይነቱ ፓሊሲ ከተገነባ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋም ይገኛል የምንለው ፋይዳ ምንድነው?
ህወሓት በገሀድ በጠላትነት የፈረጃቸው የአገራችን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ መምህራንና ሠራተኞች ይህንን አሳሳቢ ጉዳይ በአጽንኦት እንዲመለከቱ ግንቦት 7፣ የፍትህ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ያሳስባል። ትውልድንም የትምህርት ሥርዓቱንም የማዳን ግንባር ቀደም ኃላፊነት በተማሪዎችና በመምህራን የወደቀ ሸክም ነው ብሎ ግንቦት 7 ያምናል። መላው የትምህርት ሥርዓት ለአንድ ፓርቲ የምርጫ ውድድር መሣሪያነት ሲውል ማየት እና የዩኒቨርስቲ ፕሬዚዳንቶች የሥራ አፈፃፀም የሚወሰነው ለገዢው ፓርቲ ባስገኙት ድምጽ ብዛት ነው መባሉ፤ እነሱም ይኸንን ተቀብለው መሥራት መቀጠላቸውን የመሰለ አሳፋሪ ነገር በአካዳሚያ ውስጥ የለም። የከፍተኛ ትምህርት ተቋሞቻችን ይህን ውርደት መቀበል የለባቸውም። ሰነዱ ህወሓት ከፍተኛ ትምህርትን የሚመለከትበት ዕይታ ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ነውና ለምርጫ ወቅት ብቻ የተዘጋጀ የአጭር ጊዜ መመሪያ ተደርጎ መወሰድ የለበትም። ይህ ሰነድ ህወሓት፣ ተማሪዎችንና መምህራንን እንደጠላት፤ ተቋማቱን ደግሞ ጠላትን እንደመቆጣጠሪያ መሣሪያ እንደሚመለከት፤ ይህ ዕይታው ደግሞ ቋሚ መሆኑ በግልጽ ያሳያል። በህወሓት ዕይታ ከተገነቡ ተቋማት ምን ዓይነት ትምህርት ይገኛል?
የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ መምህራን፣ የትምህርት ኃላፊዎችና ፕሬዚዳንቶች ሆይ! ለገዛ ራሳችሁ ክብር፣ ለአካዳሚ ነፃነት፣ ለትውልድ ስትሉ በዚህ መመሪያ ላይ አምጹ! “እንቢ፣ አሻፈረን፣ በዚህ መመሪያ አንገዛም” በሉ! የኢትዮጵያ ሕዝብ ከጎናችሁ ይቆማል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!

ታሪክን ማደብዝዝም ማጥፋትም አይቻልም!


በአለማችን በተለይ አፍሪካ ዉስጥ የአገርን ብሄራዊ ኃብት የሚዘርፉ፤የህዝብን መብት የሚረግጡና አገርን እነሱ ባሰኛቸዉ አቅጣጫ ብቻ ይዘዉ የሚነጉዱ አያሌ ፈላጭ ቆራጭ መንግስታት አሉ። እነዚህ ህዝብን የሚበድሉ መንግስታት ሁሉም በጥቅሉ አምባገነን ይባሉ እንጂ በመካከላቸዉ ጎላ ብሎ የሚታይ ትልቅ ልዩነት አለ። ሀኖም የቱንም ያክል ልዩነት ቢኖርም እንደ ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች እንመራዋለን የሚሉትን ህዝብ የሚንቁና የኛ ነዉ የሚሉትን አገር የሚጠሉ አምባገነን መንግስታት የሉም፤ በታሪክም ኖረዉ አያዉቁም። አምባገነን መንግስታት የስልጣን ዘመናቸዉን ለማራዘምና ከስልጣን ጋር ተያይዞ የሚመጣዉን ክብር፤ ዝናና ጥቅማ ጥቅም እንዳይቋረጥ ሲሉ የሚቃወማቸዉንና ለስልጣን ዘመናቸዉ አደጋ ነዉ የሚሉትን ሁሉ ያስራሉ፤ ይደበድባሉ ወይም ይገድላሉ። እነዚህን ነገሮች የወያኔ መሪዎችም ያደርጋሉ፤ ነገር ግን በወያኔና በሌሎቹ አምባገነን አገዛዞች መካክል እጅግ በጣም ትልቅ ልዩነት አለ። ለምሳሌ ወያኔዎች ዘረኛ አምባገነኖች ናቸዉ፤ የወያኔ መሪዎች ኢትዮጵያን እንደ ጥገት ላም አንጂ እንደ አገራቸዉ አይመለከቱም። ከዚህ በተጨማሪ ኢትዮጵያን፤ ህዝቧንና ታሪኳን ይንቃሉ፤ ያንኳስሳሉ።
ባለፉት አምስትና ስድስት አመታት በግልጽ እንደተመለከትነዉ የወያኔ መሪዎች የኢትዮጵያን ገበሬ ከመሬቱ አፋናቅለዉ ለምለም መሬቱን ለባዕዳንና ለህወሓት የጦር መኮንኖች ሰጥተዋል። መሬቴንና ቤቴን አልለቅም ብሎ የተቀናቀናቸዉን ደግሞ በጅምላ ገድለዋል። በከተሞች ዉስጥም ከተሜዉን ምንም ካሳ ሳይከፍሉት ዕድሜ ልኩን ከኖረበት ቤቱ እያፈናቀሉ ከነቤተሰቡ ሜዳ ላይ ጥለዉት መሬቱን ባለኃብት ለሚሏቸዉ የወያኔ ባለሟሎች ሰጥተዋል። በአጠቃላይ የወያኔ መሪዎች በኢትዮጵያ አንድነት፤ በታሪኳና በህዝቧ ላይ እንዲህ ነዉ ተብሎ ለመናገር የሚዳግት ትልቅ በደል ፈጽመዋል። ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች በእናት አገራችን ላይ ያደረሱት በደል ተዘርዝሮ የሚያልቅ አይደለምና ዛሬ ወደዚያ ዝርዝር ዉስጥ አንገባም፤ ዛሬ ትኩረት የምንሰጠዉ ወያኔ ደግሞ ደጋግሞ ከዘመተባቸዉና ሙሉ ኃይሉን ካሳረፈባቸዉ የአገራችን እሴቶች አንዱ ታሪካችን ነዉና የዛሬዉ ቆይታችን በዚሁ በታሪካችን አካባቢ ይሆናል።
ታሪክ በአንድ አገር ዉስጥ እያንዳንዱ ትዉልድ ከሱ የቀደመዉ ትዉልድ በግል፤ በቡድንና በማህበረሰብ ደረጃ የተጓዘበትን መንገድ ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ካለፈዉ የምንማርበትና የወደፊቱን ጉዟችንን ለመጀመር በመረጃነት የሚያገለግለንን እዉቀት የምናገኝበት የጥበብ ድርሳን ነዉ። የማንም አገር ታሪክ ዉብ ሆኖ የሚያምርና የማያምር ሁለት ገጽታዎች አሉት፤ የማያምረንን የታሪክ ጠባሳ ወደ ኋላ ሄደን ማከም በፍጹም እንደማንችል ሁሉ የወደፊቱን ታሪካችንንም የብዙ ማህበረሰባዊ መስተጋብሮች ዉጤት ነዉና ያሰኘንን ቅርጽና ይዘት ልንሰጠዉ አንችልም። የታሪክ ዋናዉና ትልቁ ቁም ነገር የታሪኩ ባለቤት የሆነዉ ማህብረሰብ እራሱን ወደ ኋላም ወደ ፊትም የሚመለትበት መስኮት መሆኑ ነዉ። ምንም አይነት ታሪክ የሌለዉ ህብረተሰብ የለም፤ ካለም ከየት አንደመጣና ወዴት አንደሚሄድም አያዉቅም።
አገራችን ኢትዮጵያ ረጂምና ጥንታዊ ታሪክ ካላቸዉ ጥቂት አገሮች ዉስጥ አንዷ ናት። ይህ ረጂም ታሪካችን ደግሞ አንገት ቀና የሚያስደርግ የድልና የገድል ታሪክ አንደሆነ ሁሉ አንገት የሚያስደፋ የግፍና የበደል ታሪክም አለበት። የዛሬዉ ትዉልድ ኢትዮጵያዊ ካለፈዉ ታሪኩ ከበደሉም ከገድሉም ተምሮ የወደፊት አካሄዱን ከሞላጎደል መቆጣጠር የሚችል እድለኛ ትዉልድ ነዉና አባቶቹ ባቆዩለት ታሪክ ሊኮራ ይገባል። አንድ ህዝብ በታሪኩ እንዲኮራ ደግሞ ታሪኩ በተደጋጋሚ ሊነገረዉ ሊተረክለትና በጽሁም መልክትም በገፍ ሊቀርብለት ይገባል። የአገራችን የኢትዮጵያ ህዝብ ግን ለዚህ የታደለ አይደለም ፤ ምክንያቱም እንመራሀለን የሚሉት መሪዎቹ ታሪኩን የሚያንቋሽሹና የሚንቁ መሪዎች ናቸዉ።
ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ካደረሱትና ዛሬም በማድረስ ላይ ካሉት በደሎች አንዱና ዋነኛዉ የኢትዮጳያን ታሪክ ለባዕዳንና የታሪኩ ባለቤት ለሆነዉ የኢትዮጵያ ህዝብ አሳንሰዉና እንደ ተራ ዕቃ አቃልለዉ ማቅረባቸዉ ነዉ። የወያኔ መሪዎች አዲስ አበባን ሲቆጣጠሩ መጀመሪያ ከተናገሯቸዉ ንግግሮች አንዱ የኢትዮጵያን ህዝብ ታሪክ የመቶ አመት ታሪክ ነዉ ያሉት አስቀያሚ ንግግር ነዉ። በዚህ አባባል ላይ የጸና አቋም ካላቸዉ የወያኔ መሪዎች ዉስጥ ዛሬ በህይወት የማይገኘዉ መለስ ዜናዊና ጓደኛዉ ስብሐት ነጋ ዋና ዋናዎቹ ናቸዉ። የሚገርመዉ እነዚህ የኢትዮጵያን ታሪክ በአንድ መቶ አመት የወሰኑት ሁለት ግለሰቦች የተወለዱት የኢትዮጵያ ህዝብ የዛሬ 119 አመት በአፄ ሚኒልክ መሪነት ወራሪዉን የጣሊያን ጦር አይቀጡ ቅጣት በቀጡበት አድዋ ዉስጥ ነዉ።
ወያኔ ካለፈዉ መስከረም ወር ጀምሮ ባደበዘዘዉ ቁጥር እያሸበረቀ ያሰቸገረዉን የኢትዮጵያ ታሪክ ለማቆሸሽ ጠባሳዉ ከትዉልድ ወደ ትዉልድ የሚተላለፍ የክፋት ስራ እየሰራ ነዉ። ኢትዮጵያን የመሰለ ባለታሪክ አገር ገድሎ ለሞተዉ ዘረኛ ሰዉ ትልቅ ማዕከል በህዝብ ገንዘብ የሚያሰሩት የወያኔ መሪዎች ማስቀመጫ ቦታ ጠፋ እያሉ አያሌ ብርቅ የሆኑ የኢትዮጵያ ታሪክ መጽሀፍትን ከወመዘክር አይወጡ በችርቻሮ እየሸጡ ነዉ። እነዚህ ወያኔ የሚሸጣቸዉ መጽሐፍት የተጻፉት በተለያዪ ዘመናት ወደ ኢትዮጵያ መጥተዉ በነበሩት የእንግሊዝ፤ የፈረንሳይ፤ የጣሊያን፤ የስፔንና የጀርመን የታሪክ ጸሐፊዎች ነዉ። ከሰሞኑ ከአዲስ አበባ የሚመጡ ዜናዎች እንደሚያመለክቱት ወያኔ በዉጭ አገር የታሪክ ጸሐፊዎች የተጻፉትን የታሪክ መጽሐፍትና ተጠረዝዉ የተቀመጡ ቆየት ያሉ ጋዜጣዎችን በርካሽ ዋጋ እየቸበቸቡ የግሮሰሪ ዕቃ መጠቅለያ አድርጓቸዋል።
ይህንን አሳፋሪ የሆነ የወያኔ የመጽሐፍ ሽያጭ እንደ ተራ ወንጀል የምናልፍ ኢትዮጵያዉያን ካለን እጅግ በጣም ተሳስተናል። ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች የሚሰሩትን ስራ አበክረዉ የሚያዉቁ ሰዎች ናቸዉ፤ እያሰሩ ያሉት ስራ ደግሞ ግልጽ ነዉ። ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች የተጻፈ ታሪካችንን ብቻ ሳይሆን እያወደሙ ያሉት ባህላችንን፤ ወጋችንንና ቅርሶቻችንን ጨምር ነዉ እንዳልነበረ ያደረጉት። ለምሳሌ በብዙ የአለም አገሮች ዉስጥ ረጂም ዕድሜ ያስቆጠሩ ህንፃዎች፤ የታሪካዊ ሰዎች መኖሪያ ቤቶችና የተለያዪ የአገር ቅርሳቅርሶች ልዩ እንክብካቤ እየተደረገላቸዉ ከዘመን ወደ ዘመን እንዲተላለፉ የደረጋል። ኢትዮጵያ ወስጥ ግን ዕድሜ ለወያኔ ከፍተና ታሪካዊ እሴት ያላቸዉ ህንፃዎች በልማት ስም እንዲፈርሱ ይደረጋል። የጀግኖችን አጽም ያረፈበት የመቃብር ቦታም በግሬደር እየተደረመሰ የንግድና የችርቻሮ ቦታ ይሆናል።
ሌለዉ ወያኔ በታሪካችን ላይ የሚያደርሰዉ ጥፋት ታሪካችንን እንዳንማርና የታሪክ ተማራማሪዎቻችን በጥንታዊ ታሪካችን ላይ ምርምር እንዳያደርጉ እጅና እግራቸዉን ማሰሩ ነዉ። ለምሳሌ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዉስጥ የሚገኛዉ የታሪክ ዲፓርትመንት የኢትዮጵያን ታሪክ ማስተማር ብቻ ሳይሆን ታሪካችንን ከተለያየ አቅጣጫ በማጥናትና ምርምር በማድረግ ለታሪካችን መበልጸግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያደርግ ተቋም ነዉ። ሆኖም ይህ በተለያዪ መንግስታት ዉስጥ ለረጂም አመታት ትልቅ ስራ ሲሰራ የቆየዉ የታሪክ ዲፓርትመንት ዛሬ አለ ተብሎ መናገር በማይቻልበት አሳዛኝ ሁኔታ ላይ ይገኛል። ይህ ሁሉ የሚያሳየን ወያኔ የቀድሞ ታሪካችንን እያወደመ የሚቀጥለዉን ታሪካችንን ደግሞ በራሱ አቅጣጫ እያጣመመ በመጻፍ ላይ መሆኑን ነዉ።
ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች የኢትዮጵያን ታሪክ አስመልክቶ በአንድ በኩል የኢትዮጵያ ታሪክ የተጻፈዉ በተወሰኑ ሰዎች ከአንድ አቅጣጫ ብቻ ነዉ ሲሉ በሌላ በኩል ደግሞ የረጂሙን ዘመን የአገራችን የኢትዮጵያ ታሪክ ከአንድ ሞቶ አመታ የበለጠ ዕድሜ የለዉም እያሉ በተደጋጋሚ ተናግረዋል። ዛሬ በገፍ ለጨረታ ያቀረቧቸዉ የታሪክ መጽሐፍት ቁልጭ አድርገዉ የሚናገሩት ደግሞ ታሪካችን ከ3000 ሺ አመታት በላይ መሆኑንና የተጻፈዉም በተወሰኑ ሰዎች ብቻ ሳይሆን በተለያዪ ኢትዮጵያዉያንና የዉጭ አገር ሰዎች ጭምር መሆኑንደ ነዉ። ዛሬ ወያኔ እንደ ርካሽ ዕቃ እያወጣ የሚቸበችባቸዉ መጽሀፍት ለዚህ አሳዛኝ ዕጣ የበቁት ይህንን የወያኔ አይን ያወጣ ዉሸት ስለሚያጋልጡ ነዉ።
አገራችን ኢትዮጵያን እንወዳለን የምንል ኢትዮጵያዉያን በሙሉ ይህ በአፋችን ሁሌም የምንለዉ ቃል በተግባር የምንተረጉምበት አጋጣሚ ፊት ለፊታችን ላይ ተደቅኗል። ኢትዮጵያ አንደ ገና ዳቦ ከላይና ከታች ወያኔ ባነደደዉ ረመጥ እሳት እየተለበለበች ነዉ። ይህንን እሳት ማጥፍትና አገራችንን ከወያኔ መታደግ ካለብን ግዜዉ ነገ ሳይሆን ዛሬ ነዉ።
አያሌ ኢትዮጵያዉያን የወያኔን የመጽሐፍ ሽያጭ አስመልክቶ የወሰዱትን ቆራጥና ብልህ እርምጃ ግንቦት ሰባት የፍትህ፤ የነጻነትና፤ የዲሞክራሲ ንቅናቄ እጅግ በጣም ያደንቃል። በአዲስ አበባና በአካባቢዋ የሚገኙ አያሌ አገር ወዳድ ኢትዮጵያዉያን የአገርና የወገን ሃላፊነት ተሰምቷቸዉ ወያኔ ለጨረታ ያቀረበዉን መጽሐፍ በመግዛት የአገራቸዉን ታሪክ ለመታደግ ያደረጉት ጥረት በዋጋ ሊተመን የማይችል ትልቅ አገራዊ ስራ ነዉ። አገራችን ዛሬ ባለችበት ሁኔታ ነገ አትገኝም የሚል እምነታችን የጸና ነዉና እነዚህን የገዛችኋቸዉን መጽሀፍት በጥንቃቄ በመያዝ ሀላፊነትና የአገር አደራ ለሚሰማዉ በህዝብ የተመረጠ መንግስት አንድታስረክቡ አደራ እንላችኋለን። ከአሁን በኋላም ቢሆን የወያኔን ፀረ አገርና ፀረ ህዝብ ስራ እየተከታተላችሁ እንድታከሽፉና በሚያልፈዉ ህይወታችሁ የማያልፍ ታሪክ ሰርታችሁ ወያኔን በማሰወገዱ ዘመቻ ዉስጥ ሙሉ ተሳትፎ አንድታደርጉ አገራዊ ጥሪ እናስተላለፋለን።

Friday 21 November 2014

መምጫውን የማያውቅ መድረሻውን ያጣል


ታሪክ ለሰው ልጅ ስሩና መሠረቱ ነው።ታሪኩንና መምጫውን የማያውቅ ህዝብ መድርሻውን የማያውቅና ራሱንም ለባርነት አሳልፎ የሰጠ ይሆናል፡፡ ለክብሩ ለእርሱነቱ ለህብረቱና ለነፃነቱ ፀንቶ መቆየት እና የጥንካሬውና ተሳስሮ የመዝለቂያው ሰንሰለት ታሪኩ መሆኑ ይታወቃል፡፡
የአሜሪካ ባርያ ፈንጋዮች ትናንት በገፍ ከአፍሪካ በባርነት ያመጡዋቸው አፍሪካውያን አንድ ቀን በአንድ ቆመውና በህብረታቸው ጠንክረው ራሳቸውን ነፃ ለማውጣት እንዳይነሱ ሀ ብለው የነጠቋቸው ማንነታቸውን፤ ታሪካቸውንና መገኛቸውን ነበር፡፡ እንደ እቅዳቸውም እነሆ ዛሬ አብዛኛው ጥቁር አሜሪካዊ እኔ ማን ነኝ? መምጫዬስ ከወደየት ነው? በሚሉና በመሳሰሉ ጥያቄዎች ተተብትቦ ለምላሹ ሲውተረተር መገኘቱ፤ እንዲሁም ዛሬም ከተገዢነት መንፈስ ራሱን አላቆ በሁለት እግሩ ለመቆም ሲታትር ይገኛል፡፡
ሌላው የኢጣልያ ወራሪን ሀይል ቅስም የሰበረውና በአለም አቀፍ ደረጃ ቅሌት ያከናነበው የአድዋ ጦርነት መሆኑ ይታወቃል፡፡ ይህንንም ቅሌት በደም አጥቦ ሀያልነቱን ለአለም ለማሳየት በሞከረበት ሁለተኛው ወረራ ወቅት ከወሰዳቸው እርምጃዎች አንዱ የአድዋ ጦርነት የመሩት የአፄ ሚንሊክ ሀውልትን ከጥልቅ ጉድጓድ መቅበር እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ባጠቃላይ አንድ ህዝብ እንደ ህዝብና ሀገር ጠንክሮና በነፃነት ኮርቶ ለመኖር ብሎም ከትውልድ ትውልድ መሸጋገር መቻል ከማረጋገጫው አንዱ የትናንት ማንነቱና የመገኛ ታሪኩ መሆኑን ከላይ በምሳሌነት ያነሳናቸው ነጥቦች ያረጋግጣሉ፡፡
ታሪክ ለአንድ ህዝብ የማንነቱ መገኛ፤ የመገኛው ምንጩና መምጫውን የሚያሳይ ብቻ ሳይሆን የነገ መዳረሻውን የመመልከቻ መነፅርና ጠንክሮ የመንቀሳቀሻው ጉልበቱ ሆኖ የሚያገለግል ትልቅ መሳሪያ ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ አንድ ህዝብ ታሪኩ ከጠፋ ሊገጥመው የሚችለው ችግርና ፈተና እንዲህ በቀላሉ የሚገመት ያለመሆኑንና እንደ ህዝብ እንደ ሀገር ቀጣይነቱን በቀላሉ መፍትሄ ከማይገኝለት ፈተና ውስጥ ይከተዋል ማለት ነው፡፡
ኢትዮጵያችን ዛሬ ከመቼውም ጊዜ በከፋ ሁኔታ ህልውናዋ አደጋ ላይ የወደቀበት መሆኑ ለማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ ባለፉት 23 አመታት በዘረኞቹ የወያኔ ጉጅሌዎች እጅ ከወደቀችበት እለት ጀምሮ የኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት መገለጫ የሆኑ የታሪካችንና የባህልችን ዋና ዋና እሴቶች ዋነኛ ኢላማ ሆነዋል፡፡ ይህንንም በተደጋጋሚና በግልፅ ከወያኔው መሪ እስከ ተራ ደጋፊው የሚወረወረው በትር ያረጋግጣል፡፡ ጉጅሌዎቹ የነፃነት ምልክት የሆነውንና በዕልፍ አዕላፋት ደም መሥዋዕትነት ፀንቶ የቆየውን ሰንደቅ ዓላማ በሶ መጠቅለያ ጨርቅ ከማድረግ ጀምረው ዛሬ በምሁራን ጥረትና በእያንዳንዱ ዜጋ ድጋፍ የተሰባሰቡት የታሪኮቻችን መዛግብት በጥንቃቄ ከተቀመጡበት (ቤተ-መዛግብት) እያወጡ ከማውደምና ለስኳር መጠቅለያነት እስከ መሸጥ ደርሰዋል፡፡
ታሪካዊ ገዳማት ፈርሰዋል፤ ታሪካዊ ቅርሶች ለባእዳን አልፈው ተሽጠዋል፤ የነፃነት ታሪካችን እየተደለዘ በወያኔያዊ ዘረኛ የፈጠራ ታሪክ መተካቱ ቀጥሏል፤ ታሪካዊ ጀግኖቻችንን ማዋረድና ማውገዝ የእለት ተእለት ስራቸው ሁኗል። ወ ያኔዎች ኢትዮጵያዊነት ቅዝት ሆኖባቸዋል፤ ስለዚህም ቀንደኛ ጠላታቸው አድርገው ፈርጀውታል፡፡ ይህ የዘረኝነትና የዘረፋ ስርዓታቸው ውሎ ማደር የሚረጋገጠው ኢትዮጵያዊነት መመታት ሲችል ብቻ ነው ብለውም በፅኑ ያምናሉ፡፡ ለዚህም ነው ኢትዮጵያዊነታችንን ሊያዳክም ብሎም ሊያጠፋ ይችላል ብለው የገመቱትን ሁሉ ከመፈፀም የማይመለሱት፡፡ ለዚህም ነው በስንት ጥረትና በብዙዎች ድካም ተሰባስቦና ተደራጅቶ የቆየውን የታሪክ መዛግብትና መፅሀፍት ከቤተ-መዘክር አውጥቶ በኪሎ ለመቸብቸብ የበቁት፡፡
ታዲያ ኢትዮጵዊ ነን የምንል ሁሉ ዘሬም እንደትናንቱ ይህን በማንነታችን ላይ የሚደረግ የጥፋት ዘመቻ ለማስቆም መነሳት ግድ ይለናል። እየተፈፀመ ያለው የታሪክ ማጥፋት ዘመቻ ለነፃነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ከምናደርገው ትግል እኩል ጎን ለጎን ለታሪካዊ ቅርሶቻችንና መዛግብቶቻችን ከጥፋት የመከላከልና የማዳን ስራ የመስራት የትውልድ ኃላፊነት አለብን፡፡ አለበለዚያ መምጫውን የማያውቅ መድረሻውን አያውቅምና የምናደርገው የነፃነት ትግል የተሟላ ውጤት ማስገኘቱ ጥያቄ ውስጥ መግባቱ አይቀሬ መሆኑን መገንዘብ ይገባናል፡፡ ተገንዝበንም ወያኔን በቃህ ልንለው ይገባል፡፡
በመጨረሻም ጂኦርጅ ኦርዌል ‘The most effective way to destroy people is to deny and obliterate their understanding of their own history” ብሎ ጽፎ ነበር። ህወሃቶች የዚህ ፍልስፍና ተከታዮች መሆንን በመምረጥ ለራሳቸው ውረደትን ፤ለአገራቸውም ውደቀትን ተመኝተዋል። ኢትዮጵያችን መንግስት በጠላትነት ተሰልፎ ከአገራችን ከህዝብና ለአገሪቷ እሴቶች ጋር የሚዋጋበት አገር ሁናለች። ህወሃት በብዙ መልኩ ሲታይ የኢትዮጵያ ቀንደኛ ጠላት መሆንን የመረጠ ቡድን ነው። የህወሃት በኢትዮጵያ ላይ በጠላትነት መቆሙ ያስቆጣቸው ወጣቶች እምቢ ለአገሬ፤ እምቢ ለክብሬ ብለው ተነስተው ኢትዮጵያን ነፃ ለማውጣት ተሠማርተዋል።ግዜው ከእነዚህ ወጣቶች ጎን የምንቆምበትም ጭምር ነውና ተነሱና ለነፃነታችንና ለአገራችን ዝና ለህዝባችን ክብር አብረን ታግለን ጠላትን የመረጠውን ህወሃትን እናስወግድ እና ንፁህ አገር እንፍጠር።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !!

Sunday 16 November 2014

እንግሊዝ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌን በተመለከተ ደብዳቤ መጻፏን ወያኔ አረጋገጠ


የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሮን አቶ አንዳርጋቸው ፅጌን በተመለከተ ለወያኔዉ ጠቅላይ ሚኒስትር ደብዳቤ መጻፋቸውንና ወያኔም አቋሙን ግልጽ ማድረጓን የወያኔዉ ኮሙዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤት ሚኒስትሩ አቶ ሬድዋን ሁሴን ተናገረ። ሬድዋን በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ባለፈዉ ማክሰኞ በሰጠዉ ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ዴቪድ ካሜሩን ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደብዳቤ መጻፋቸውን የተለያዩ የውጭ ሚዲያዎች መዘገባቸውን ሰምቻለሁ ካለ በኋለ “ለምን ጻፉ ማለት አይቻልም፤ ጥያቄዉ መሆን ያለበት ምን መለሳችሁ ነው፤” በማለት የተለመደ የማጭበርበሪያ ቃላት ደርድሯል።
የተለያዩ የእንግሊዝ ሚዲያዎች ኢትዮጵያ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ላይ ቀደም ሲል የተፈረደውን የሞት ቅጣት እንዳትተገብር እንዲሁም ኢትዮጵያ ለሚገኘው የእንግሊዝ ኤምባሲ አቶ አንዳርጋቸውን የመጐብኘት ቋሚ ፈቃድ እንዲሰጥ በደብዳቤያቸው መጠየቃቸውንም ሬድዋን ሁሴን ተናግሯል።
ለዴቪድ ካሜሮን ደብዳቤ መልስ መሰጠቱን ያረጋገጠዉ ሬድዋን፣ “በተጨባጭ የተፈረደበትን ግለሰብ ነው የያዝነው፤ እንዲህ ብታደርጉት ባታደርጉት ብሎ ማንሳት ይቻላል። ምክንያቱም እነሱም የሚመለከታቸው በመሆኑ። በዚህ ምክንያት ግን የእኛ መልስ በራሳችን ሕግ መሠረት ዓለም አቀፍ ሕጉም በሚለው መሠረት የምናደርገውን እናደርጋለን፤” ብሏል። ኢትዮጵያ የምትተገብረው የራሷን ሕግ መሆኑን የገለጹት አቶ ሬድዋን፣ “ከነጭም ከጥቁርም የሚመጣን ደብዳቤ ተንተርሰን ምንም አንተገብርም፤” ብሏል። ከዚህ በተጨማሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሮን ደብዳቤ ጽፈው፣ በኢትዮጵያ በኩልም መልስ ተስጥቷል ያለዉ ሬድዋን ሁሴን በደብዳቤው የቀረቡ ጥያቄዎች ቅሬታ እንዳላስነሱ ሁሉ መልሱም ቅሬታ አያስነሳም የሚል ተስፋ በኢትዮጵያ በኩል መኖሩን ተናግረዋል።
“እነሱ ዜጋዬ ነው ብለዋል፤ የእነሱ ዜጋ እንደ ቼ ጉቬራ ነፃ አውጣ ተብሎ ኢትዮጵያ ውስጥ አልተላከም። የእነሱ ዜጋ ከነበረ የእንግሊዝን ዴሞክራሲ ይበልጥ ለመጨመር መታገል ይችል ነበር። ነገር ግን በኢትዮጵያ በቅጥር ነብሰ ገዳይነት ካልተሰማራ በስተቀር ሌላ ሚና አልነበረውም፤” ብለዋል።

የሰንደቅ አላማችን ጠላት ወያኔና ወያኔ ብቻ ነዉ!



ሰንደቅ አላማ ለአንድ አገር ህዝብ የኩራት፤ የአልበገር ባይነት፤ የአንድነትና የታሪክ ተከታታይነት ምልክት ነዉ። ሰንደቅ አላማ በአንድ በኩል የወደፊቱን ብሩህ ተስፋ ክወዲሁ እያሳየን እየዟችሁ የሚለን፤ በሌላ በኩል ደግሞ በምናብ ወደኋላ እየወሰደን የድልና የመስዋዕትነት ታሪላችንን የሚያስታዉሰን የነጻነት፤ የሠላምና የብሩህ ተስፋ ማህደር ነዉ። የአገራቸን የኢትዮጵያ አረንጓዴ፤ ቢጫና ቀይ ሰንደቅ አላማ ትናንትናና ከትናንት ወዲያ በተስፋፊዎች አለመደፈራችንን ብቻ ሳይሆን ዛሬም ዘረኞች የጫኑብንን የመከራ ቀንበር በቆራጥነት ሰብረን ነገና ከነገ ወዲያ የነፃነት አየር እንድንተነፍስ አስረግጦ የሚነግረን የአንድነታችን፤ የተገጋድሏችንና የድላችን ልዩ ምልክት ነዉ። አንድን ኢትዮጵያዊ ሰንደቅ አላማ ላንተ ምንህ ነዉ ብለን ብንጠይቀዉ ጥያቄዉን ዕድሜህ ስንት ነዉ ተብሎ እንደሚጠየቅ አንድና ሁለት ቃል ብቻ ተናግሮ አይመልስም። ሰንደቅ አላማም በአንድና በሁለት ቃላት ምንነቱ የሚገለጽ ተራ ቃል አይደለም። ኢትዮጵያዉያን ተማሩ አልተማሩ፤ ደሃ ሆኑ ኃብታም ፤ወንጀለኛ ሆኑ ወይም ሠላማዊ ለአገራቸዉ ሰንደቅ አላማ የተለየ ቦታ አላቸዉ። ሰዎች የአገራቸዉን ሰንደቅ አላማ የሚወዱትና ለሰንደቅ አላማዉ በክብር መዉለብለብ የህይወት መስዋዕትነት የሚከፍሉት ስለታዘዙ ወይም ስለ ሰንደቅ አላማዉ ተነግሯቸዉ አይደለም። በእርግጥም የሰንደቅ አላማ ክብርና የአገር ፍቅር ለሰዎች ሰንደቅ አላማዉን አክብሩ፤ አገራችሁን አፍቅሩ እየተባለ የሚነገር ነገር አይደለም። አገርንና ወገንን ማክበርና መዉደድ ሰንደቅ አላማን ከማክበርና ከማፍቀር ጋር በቀጥታ የተገናኘ ነዉ።የሰንደቅ አላማ ልዪ ክብርና የአገር ፍቅር ሰዎች ተወልደዉ ከሚያድጉበት ማህበረሰብ፤ ከቤተሰብ፤ ከጎረቤትና ከጓደኛ እንደ ምግብና እንደ ዉኃ እየበሉና እየጠጡ የሚያገኙት የሰዉነትና የዜግነት መገለጫ ታላቅ እሴት ነዉ።
ለዚህም ነዉ የማንም አገር ዜጋ አገሩ ዉስጥ ቢኖር ወይም ካገሩ ዉጭ፤ ቢታሰር ባይታሰር፤ ሀብታም ቢሆን ወይም ደሃ፤ የኔ ነዉ የሚለዉን የእናት አገሩን ሰንደቅ አላማ በፍጹም የማይረሳዉ። ከአገራቸዉ ዉጭ የሚኖሩ ሰዎች ደግሞ በተለይም ኢትዮጵያዉያን በተለያዩ ምክንያቶች የሚኖሩባቸዉን አገር ዜግነት ቢወስዱ እንኳን ሰንደቅ አላማቸዉን ባዩና ባስታወሱ ቁጥር የሚሰማቸዉ አገራዊ ስሜት እጅግ በጣም ከፍተኛ ነዉ – እንዲያዉም ከአገራቸዉ ተሰድደዉም ሆነ በልዩ ልዩ ምክንያቶች ከአገራቸዉ ዉጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዉያን ሰንደቅ አላማቸዉን ባዩ ቁጥር የአገራቸዉ፤ የወንዛቸዉ ፤ ተወልደዉ ያደጉበት መንደርና የልጅነት ትዝታቸዉ ባአይናቸዉ ላይ እየመጣ ዕንባ በዕንባ ይተናነቃሉ። ሰንደቅ አላማ ለአንድ አገር ህዝብ አንድ ነገር ነዉ፤ ብዙ ነገር ነዉ፤ ሁሉም ነገር ነዉ። ሰንደቅ አላማ ህዝብን ያስተባብራል፤ ያከባብራል፤ ያዋድዳል፤ መስዋዕትነትን፤ ፍቅርንና ብልፅግናን ያመለክታል።
ዛሬ የሰንደቅ አላማችንን ጉዳይ አቢይ የመወያያ አርዕት አድርገን የወሰድነዉ አለምክንያት አይደለም። በአገር ጥላቻቸዉና በስንደቅ አላማ ንቀታቸዉ የሚታወቁት የወያኔ ዘረኞች “የአብዬን ወደ እምዩ” እንዲሉ ሰንደቅ አላማቸዉ ተዋርዶ ከሚያዪ የቁም ሞታቸዉን የሚመር ትን ዉድ የኢትዮጵያ ልጆች ባንዲራዉን አዋረዱበለዉ መናገራቸዉን ስለማን ነዉ። ኢትዮጵያን ጨምሮ ብዙ አገሮች ተስማምተዉ የሚያከብሩት አለም አቀፉ የሰንደቅ አላማ አያያዝ ፕሮቶኮል በአለም አቀፍ መድረኮች ላይ የሁሉም አገሮች ሰንደቅ አላማ በእኩል ደረጃ መቀመጥና መሰቀል አለበት፤ አንድ ላይ መሰቀልና አንድ ላይ መዉረድ አለበት ይላል። ይህንን ፕሮቶኮል ረስቶና ሰንደቅ አላማችንን ንቆ በአለም አቀፍ መድረክ ላይ ከሌሎች አገሮች መሪዎች ጋር የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ እንደ አለባሌ ዕቃ ዘቅዝቆ ይዞ ያዋረደዉ ወያኔዎች “ታላቁ መሪ” ብለዉ የሚጠሩት ነገር ግን የለየለት የአገርና የህዝብ ጠላት የሆነዉ ዘረኛዉ መለስ ዜናዊ ነዉ። የህወሓትን ባንዲራ በየቦታዉ እየሰቀሉ የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ ተራ ጨርቅ ነዉ ብለዉ የሸቀጥ መጠቅለያ ያደረጉትም መለስ ዜናዊና ጓደኞቹ ናቸዉ። ዛሬ ደማቅ ሰንደቅ አላማዉን አስመልክቶ በወያኔና በኢትዮጵያ ህዝብ መካከል ያለዉ ትልቅ ልዩነት ትክክለኛዉና ህዝብ የኔ ነዉ ብሎ የተቀበለዉ የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ የትኛዉ ነዉ የሚለዉ ጥያቄ ላይ ነዉ አንጂ ባንዲራዉን ማክበር አለማክበር ወይም ማዋረድ ላይ አይደለም።
የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ የእናት አገራችንን የኢትዮጵያንና የህዝቦቿን ታሪካዊ ተከታታይነትና ዘለዓለማዊነት አጉልቶ የሚያሳየን ከሁላችንም በላይ የገዘፈ ግዙፍ አርማ ነዉ፤ ይህ ማለት ደግሞ ሰንደቅ አላማችን ያቻትና ብሎ እንደሚያሳየን አገር አንደ ኢትዮጵያ ሙሉ ህልዉና ያለዉ ህያዉ አካል ነዉ ማለት ነዉ። ሰንደቅ አላማችንን የምንወደዉና የምናከብረዉም ህያዉ አገራችንን የሚወክል ህያዉ አካል በመሆኑ ነዉ። መለስ ዜናዊንና ስብሀት ነጋን የመሳሰሉ በጣት የሚቆጠሩ የትዉልድ ጭንጋፎች ለራሳቸዉ አገር ሰንደቅ አላማ ደንታ ላይኖራቸዉ ይችላል። የኢትዮጵያ ህዝብ እንዳለ ግን የህልዉናዉና የአንድንቱ መገለጫ የሆነዉን ሰንደቅ አላማ አይንቅም ወይም አያዋርድም፤ አንድ ህዝብ ባንዲራዉን የማይቀበልና የማያከብር ከሆነ ባንዲራዉ አይወክለዉም ማለት ነዉ፡ ኢትዮጵያ ዉስጥ ዛሬ ያለዉ እዉነታም ይሄዉ ነዉ፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ወያኔ ባዕድ አካል የለጠፈበትን ባንዲራ የኔ ነዉ ብሎ አልተቀበለዉም ወይም ባንዲራዉ ይወክለኛል ብሎ አያምንም።
ዘርዓይ ደረስ በ1937 ዓም ሮም ዉስጥ የፋሺስት ጣሊያኖችን ጭንቅላት በገዛ አገራቸዉ እንደ ቅጠል እየጨረገደ ከጣለ በኋላ በጣሊያኖች ጥይት ቆስሎ ሲያዝ የተናገዉ የመጨረሻ ቃል ይህ የጣሊያኖች ባንዲራ ይዉረድና የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ ይሰቀል የሚል የጀግንነትና የአገር ፍቅር ቃል ነበር። ጀግናዉ አብዲሳ አጋ በጣሊያን በረሃዎች ጣሊያኖችን እያሳደደ ሲገድል የኢትዮጵያ ባንዲራ ከአጠገቡ አልተለየችም። በቀዳማዊ ኃ/ስላሤና በደርግ ዘመነ መንግስት ተማሪዎች ጧት ወደ ክፍል ከመግባታቸዉ በፊት ተሰልፈዉ የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ በክብር ይሰቅሉ ነበር፤ ማታም ወደ ቤታቸዉ ከመሄዳቸዉ በፊት ጧት በክብር የሰቀሉትን ባንዲራ በክብር አዉርደዉ ነበር ወደየቤታቸዉ የሚሄዱት። ዛሬ የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ ጨርቅ ነዉ ብለዉ የተሳደቡና በዚህ ሰንደቅ አላማ ከገበያ የገዙትን ሸቀጥ እየጠቀለሉ አስራ ሰባት አመት የከረሙ ምናምንቴዎች ናቸዉ በሰንደቅ አላማ ክብርና በአገር ፍቅር ታንጾ ያደገዉን ኢትዮጵያዊ ሰንደቅ አላማዉን አዋረደ እያሉ የአዞ እምባ የሚያነቡት።
ሰንደቅ አላማ በዜጎች ልብ ዉስጥ አንደ እሳት የሚቀጣጠል የአገር፤ የህዝብና የዜግነት መገለጫ የሆነ ታላቅ አርማ ነዉ። ይህ አርማ ደግሞ ከእኛነታችንና ከህልዉናችን ጋር የተጣበቀ አርማ ነዉና መንግስት በተለዋወጠ ቁጥር አይለዋወጥም። ዛሬ ወያኔ የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር የገባዉ የማይታረቅ ቅራኔም የሚመነጨዉ ከዚሁ ከወያኔ ግራ የተጋባ እዉነታ ነዉ። የዚህ ዘመን ትዉልድም ሆነ ለዚህ ዘመን ትዉልድ አገርና ሰንደቅ አላማ አስረክቦ ያለፈዉ የቀድሞዉ ትዉልድ ሰንደቅ አላማዬ ብሎ የሚጠራዉና ወያኔ የኢትዮጵያ ባንዲራ እያለ የሚጠራዉ ነገር የተለያዩ ናቸዉ።
ባለፉት 75 አመታት አራት ኪሎ ቤ/መንግስትን የተቆጣጠሩት ሦስት ኃይሎች ማለትም የቀኃስ፤ የደርግና የወያኔ አገዛዞች ሁሉም የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ ከራሳቸዉ ጋር ለማያያዝ ሞክረዋል። በንጉሡና በደርግ ዘመነ መንግስት የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ የይሁዳ አንበሳና የወታደራዊዉ መንግስት አርማ ነበረበት፤ ሆኖም እነዚህ ሁለት አርማዎች ያረፈበት የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ በቤተመንግስትና ንጉሡና ፕሬዚዳንቱ በሚጓዙባቸዉ ኦቶሞቢሎች ላይ እንጂ ሌላ ቦታ አይታዩም ነበር። በመላዉ አገሪቱ በየቀኑ ጧት እየወጣ ማታ ሲመሽ የሚወርደዉና በየግለሰቦች ቤት የሚገኛዉ ሌጣዉ አረንጓዴ፤ ቢጫና ቀዩ ሰንደቅ አላማ ነበር። የኢትዮጵያ ህዝብም ሰንደቅ አላማዬ ነዉ ብሎ የሚያምነዉና የሚቀበለዉ ይህንኑ ምንም አይነት ባዕድ አካላ የሌለበትን አረንጓዴ፤ ቢጫና ቀይ ሰንደቅ አላማ ነዉ።
ወያኔዎች ጫካ ዉስጥ ሆነዉ የትጥቅ ትግል በሚያካሄዱበት ወቅት ያነገቡትና ነጻ አወጣን ባሉበት ቦታ ሁሉ የሰቀሉት የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ ሳይሆን የህወሓትን ባንዲራ ነበር። ከብዙ መረጃዎች እንደተረዳነዉ ወያኔዎች የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ አንደ ተራ ጨርቅ ቆጥረዉ ዕቃ መጠቅለያ አድርገዉት ነበር፤ ይህ ደግሞ የለየለት የጥላቻና የንቀት ምልክት ነዉ።
በአርግጥም ዋና ዋናዎቹ የወያኔ መሪዎች እነ ነመለስ ዜናዊና እነ ስብሐት ነጋ ኢትዮጵያንና የኢትዮጵያን ህዝብ ይጠሉ ስለነበር ለነሱ ትልቁ ቁም ነገር ህወሐትና የዘረኝነት ምልክት የሆነዉ የህወሓት ባንዲራ ነዉ እንጂ ኢትዮጵያና የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ አልነበረም። ይህ ፀረ ህዝብና ፀረ አገር ባህሪያቸዉ ደግሞ ጫካ ዉስጥ ብቻ ተወስኖ የቆየ ባህሪ ሳይሆን አዲስ አበባ ገብተዉ ክህዝብ ጋር ሲቀላቀሉም በግልጽ የታየና ምን ግዜም ሊደበቅ የማይችል ባህሪይ ነዉ። የወያኔዉ ቁንጮ መለስ ዜናዊ እኛ ኢትዮጵያዉያን የምናከብዉንና የምንወደዉን ሰንደቅ አላማ “ጨርቅ” ብሎ መጥራቱ አዲስ የጀመረዉ ነገር ሳይሆን ከጫካ ይዞት የመጣዉ የተለመደ አባባል ነዉ። መለስ ዜናዊ ይህንን ጸያፍ ድፍረቱንና ፀረ ሰንደቅ አላማነቱን ለማረሳሳት የባንዲራ ቀን ብሎ ቢያዉጅም የኢትዮጵያ ህዝብ ግን ልጆቹ፤ አባቶቹ፤ አያቶቹና ቅድም አያቶቹ የተሰዉለት ሰንደቅ አላማ በአለባሌ ሰዉ አንደበት “ጨርቅ” ተብሎ የተጠራበትን ቀን ምን ግዜም አይረሳም።
ከቅርብ ግዜ ወዲህ የወያኔ ዘረኞች ኢትዮጵያዉያንን በተለይም በዉጭ አገሮች የሚኖሩ ኢትዮጵያዉያንን ባንዲራቸዉን አያከብሩም ወይም ባንዲራዉን አዋረዱ እያሉ መክስስ ጀምረዋል። በነገራችን ላይ ከወያኔዎችና ከጥቂት ሆዳም ተከታዮቻቸዉ ዉጭ የኢትዮጵያ ህዝብ አገር ዉስጥም በዉጭ አገሮችም በሰንደቅ አላማዉ ላይ ያለዉ አቋም ተመሳሳይ ነዉ። ወያኔ ሰንደቅ አላማዉ ላይ ባዕድ አካል ለጥፎ ከዛሬ ጀምሮ ሰንደቅ አላማችሁ ይህ ነዉ ብሎ አዋጅ ሲያወጣ አዋጁን የሰማለት አንድም ሰዉ አልነበረም። እንዲያዉም ህዘብ ሰላማዊ ሰልፍ ሲወጣ፤ ሰርግ ሲደግስ፤ ኳስ ጨዋታ ሲሄድና በተለያዪ ቦታዎች ደስታዉንና ኃዘኑን ሲገልጽ አንግቦ የሚወጣዉ የወያኔን ባንዲራ ሳይሆን አረንጓዴ፤ ቢጫና ቀዩን ሰንደቅ አላማ ነበር። ወያኔ የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ የቀየረዉ በጠመንጃ ሀይል እንደሆነ ሁሉ የኢትዮጵያ ህዝብ ይህንን የማይወደዉንና በሀይል የተጫነበትን ባንዲራ ተቀብሎ እንዲኖር ያደረገዉም በጠመንጃ ሀይል ነዉ።
ለመሆኑ እነሱ እራሳቸዉ የለየላቸዉ የኢትዮጵያና የኢትዮጵያዊነት ጠላት የሆኑት የወያኔ መሪዎች በዉጭ አገሮች የሚኖሩና አክርረዉ የሚቃወሟቸዉን የኢትዮጵያ ልጆች ባንዲራዉን አዋረዱ እያሉ ተደጋጋሚ ክስ የሚያሰሙት ለምንድነዉ? አንዳንድ ከህልዉናቸዉ ይልቅ ለማይጠረቃዉ ሆዳቸዉ ያደሩ ደካማ ግለሰቦችስ ይህንን የወያኔ መሠረተ ቢስ ክስ እየሰሙ አንደ ገደል ማሚቶ ደግመዉ ደጋግመዉ የሚያስተጋቡት ለምንድነዉ? አገራችን ኢትዮጵያ ሁለት የተለያዩ ባንዲራዎች ሊኖራት እንደማይችል ሁላችንም እናዉቃለን። ለመሆኑ ይህ እኛ ሰንደቅ አላማ እነሱ ባንዲራ እያልን የምንጠራዉ ነገር አንድና ተመሳሳይ ነዉ? ወያኔና በየቦታዉ ያስቀመጣቸዉ የገደል ማሚቶዎች ከሁሉም ነገር አስቀድመዉ መመለስ ያለባቸዉ ይህንን ጥያቄ ነዉ። እኛ ኢትዮጵያዉያን ከህጻንነታችን ጀምሮ የኛ ነዉ እያልን ያሳደገንን፤ የመራንን፤ አቅጣጫ ያሳየንነና በተለይ በልጅነታችን ት/ቤት እያለን ጧት በክብር ሰቅለን ማታ ላይ በክብር እያወርድን በክብር እናስቀምጥ የነበረዉን አረንጓዴ፤ ቢጫና ቀይ ሰንደቅ አላማችንን ማክበርና መዉደድ ብቻ ሳይሆን ለዚህ ሰንደቅ አላማ ዘለዓለማዊነት አንድ ህይወታችንን እንሰጣለን። ሰንደቅ አላማዉን የማያከብር ህዝብ የለም፤ እኛም ኢትዮጵያዉያን ሰንደቅ አላማችንን እንወዳለን፤ እናከብራለንም፤ የምንወደዉና የምናከብረዉ ሰንደቅ አላማ ግን ባዕድ አካል የተለጠፈበትን የወያኔን ባንዲራ ሳይሆን የነፃነታችን፤ የእንድነታችን፤ የሰላማችንና የመዋዕትነታችን ምልክት የሆነዉን አረንጓዴ፤ ቢጫና ቀዩን ሰንደቅ አላማ ነዉ። ይህንን ሰንደቅ አላማ ደግሞ እኛ ኢትዮጵያዉያን ብቻ ሳንሆን ይህንን የጥቁር ህዝብ የነጻነትና የመስዋዕትነት ታሪክ ምልክት የሆነ ደማቅ ሰንደቅ አላማ አያሌ አፍሪካዉያንም ያከብሩታል። ለምሳሌ የስምንት የአፍሪካ አገሮች ባንዲራ አቀማመጡ ይለያያል አንጂ ቀለሙ አረንጓዴ፤ ቢጫና ቀይ ነዉ፤ ከዚህ በተጨማሪ የሌሎች 23 አፍሪካ አገሮች ባንዲራ ደግሞ ቀዩና አረንጓዴዉ ቀለም አለበት። ይህ ሁሉ የሚያሳየን ሰንደቅ አላማችን የፓን አፍሪካ ባንዲራ እየተባለ በተለያዩ የአፍሪካ አገሮችም የሚከበርና የብዙ አፍሪካ አገሮች ሰንደቅ አላማ መሰረት መሆኑን ነዉ።
የወያኔ ዘረኞች ኢትዮጵያ ዉስጥ የነበሩትንና በዉጭ አገሮች የሚገኙ አማራጭ የመረጃ ምንጮች ሁሉ ጥርቅም አድርገዉ ዘግተዉ እንደቤት ዉስጥ ዕቃቸዉ በሚቆጣጠሩት ቴሌቪዥን፤ ሬዲዮና ጋዜጣ “በሬ ወለደ” አይነት ዉሸታቸዉን ጧትና ማታ በተደጋጋሚ አየተናገሩ ለግዜዉም ቢሆን ህዝብን ማደናገር ይችሉ ይሆናል። ሰንደቅ አላማዉን የሚወደዉንና የሚያከብረዉን ኢትዮጵያዊም እነሱን ስለተቃወመ ብቻ ባንዲራዉን አዋረደ እያሉ ህዝብን ሊያታልሉ አንዳንድ ወደ ገባዎችንና ጥቂት የዋሆችን ሊያሳምኑ ይችሉ ይሆናል። ሆኖም የኢትዮጵያን ህዝብ እንወዳለን ፤ ለኢትዮጵያ አንድነት እንቆማለን፤ የዚህ አንድነት ምልክት የሆነዉን ሰንደቅ አላማም እናከብራለን አያሉ ታቦት ተሸክመዉ ቢምሉም የሚያምናቸዉ ቀርቶ ከጉዳይ ቆጥሮ የሚሰማቸዉ አንድም ዜጋ የለም። የወያኔ ዘረኞችና ቡችሎቻቸዉ የሚባቸዉ ቢሆን ኖሮ ዉስጣችን ያለዉን ከፍተኛ የአገር፤ የወገን፤ የባንዲራና የሉዓላዊነት ስሜት ደግመን ደጋግመን እንነግራቸዉ ነበር፡ ሀኖም እነሱን ከማስወገድ ጀምሮ አገራችንን እስከማረጋጋት ድረስ ብዙ አስቸኳይ የሆነ አገራዊ አደራና አገራዊ ስራ ይጠብቀናልና ለዛሬዉ እዚህ ላይ እናብቃ።
የኢትዮጵያ ህዝብ ትግል ያሸንፋል!

Saturday 15 November 2014

ጊዜው የሕዝባዊ እምቢተኝነት ነው!!!



በአሁኑ ወቅት በአገራችን በከተሞችና በገጠሮች እየታዩ ያሉ ምልክቶችን በጥንቃቄ የመረመረ ማንኛውም ሰው የሚከተሉትን መታዘቡ አይቀርም።
በአንድ በኩል፣ ወያኔ የተወገደባት፣ ፍትህ የሰፈነባትና የበለፀገች ኢትዮጵያ እውን ሆና የማየት ተስፋችን እየለመለመ ነው። በዚህም ምክንያት ኢትዮጵያ ዉስጥ ለረጂም ዓመታት በሕዝብ ላይ ሰፍኖ የነበረው የፍርሀት ደመና እየገለጠ በመሆኑ ተዘግተው የቆዩ አንደበቶች መናገርና “ይኸ ሁሉ ግፍ ለምን?” ብለው መጠየቅ ጀምረዋል። ይህንን መነቃቃት በአስተሳሰብም፣ በተግባርም፣ በኪነጥበብም እያየነው ነው። የኢትዮጵያ ወጣቶች ለውጥ በአገራችን ሊመጣ እንደሚችል ከማመን አልፎ ራሳቸውን በለውጥ አምጭ ኃይልነት መመልከት ጀምረዋል። በርካታ ወጣቶች ወያኔን በትጥቅ ለመገዳደር የወሰኑ ወገኖቻችንን እየተቀላቀሉ በዚህም ምክንያት ጉልበታቸውን እያፈረጠሙ ነው። የለውጡ እርሾ ከሲቪሉ አልፎ በመከላከያ ሠራዊቱ እና በኢሕአዴግ ድርጅቶች ውስጥም እየተብሰለሰለ ነው። የኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት፣ ህወሓት ኢትዮጵያን ለማጥፋት የሚጠቀምበት ኃይል መሆኑ እያበቃ በአንፃሩ የትግሉ አጋር የሚሆንባቸው ሁኔታዎች እየታዩ ነው። በሁሉም የሠራዊቱ ክፍሎች ጉምጉምታው ወደ ጩኸት እየተቀየረ በመሆኑ ሠራዊቱ በአለቆቹ ላይ የሚነሳበት ጊዜ እሩቅ አይደለም። በተለያዩ ምክንያቶች ህወሓትን ወይም ህወሓት የፈጠራቸውን ድርጅቶች የተጠጉ በአጠቃላይ ኢሕአዴግ በሚባለው ስብስብ ውስጥ የሚገኙ ወገኖቻችንም “ለመሆኑ ማንን ነው እያገለገልን ያለነው?” ብለው በመጠየቅ ላይ ናቸው። በዚህም ምክንያት ወያኔ ውስጡ እየተረበሸ ነው። ከኢትዮጵያም ውጭ በሚገኘው ኢትዮጵያዊ ዘንድ ያለው ቁጣና ዝግጁነት ከወትሮው እጅግ የላቀ ነው። በአጭሩ፣ በሁሉም አቅጣጫ፣ ደረጃ በደረጃ የሕዝባዊ እምቢተኝነት እንቅስቃሴዎች ተጀምረዋል።
በአንፃሩ ደግሞ፣ የጨለማ ንጉሥ የሆነው ወያኔ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብን ወደ ፍርሀት ቆፈን ለመመለስ እስሩን ከመቸውም በላይ ያጧጧፈበት ጊዜ ነው። በትግራይ፣ በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በደቡብ፣ በአፋር በሶማሊ … በመላው ኢትዮጵያ ብሩህ ራዕይ የሰነቁ ወጣቶችና አዛውንት ታድነው እየታሰሩ ናቸው። የወያኔ እስር ቤቶች በአርቆ አስተዋይ ዜጎቻችን ተሞልተዋል። ወትሮም ከፍተኛ የነበረው ስደት ብሶበታል፤ ለእውነት በጽናት የቆሙ ጋዜጠኞች ወይ ታስረው፣ አልያም ተሰደው አልቀዋል። የወያኔ የግዴታ ስልጠና አገሩን እያመሰው ነው። የኢትዮጵያዊያን ኑሮ በእጦቶች የታጀበ ሆኗል። የነፃነት እጦት፣ የፍትህ እጦት፣ የመብራት እጦት፣ የስኳር እጦት፣ የዘይት እጦት፣ የታክሲ እጦት፣ የመኖሪያ ቤት እጦት፣ እጦት፣ …. እጦት።
እነዚህ ሁለት ተፃራሪ እውነታዎች ሁለት ተፃራሪ ኃይሎች ለወሳኝ ፍልሚያ ፊት ለፊት መፋጠጣቸዉን በግልጽ ያሳያሉ። ዛሬ አገራችን ኢትዮጵያ ውስጥ ነፃነትና ባርነት፣ ፍትህና ጭቆና፣ ደስታና ሀዘን፣ ተስፋና ተስፋ መቁረጥ፣ ብልጽግናና ድህነት፣ እውቀትና ድንቁርና፣ ብርሃንና ጨለማ፣ ለወሳኝ ግጥሚያ ተፋጠዋል። ይህ ፍጥጫ የኢትዮጵያን የወደፊት እጣ ፈንታን በመወሰን ረገድ አቢይ ሚና የሚኖረው ወሳኙ ግጥሚያ – ሕዝባዊ እምቢተኝነት – መጀመሩን አብሳሪ ነው። የነፃነት፣ የፍትህ፣ የተስፋ፣ የብልጽግና፣ የእውቀትና የብርሃን ወገኖች ነን የምንል ኢትዮጵያዊያን ሁሉ ይህንን ፍልሚያ በድል መወጣት ግዴታችን ነው።
ወያኔ ታጋዮችን ቢያስር ትግሉን አያስርም። በእጦት ኑሮዓችን በማመሰቃቀል በድህነት ሊያንበረክከን ቢሻም፣ በፍጹም አንበረከክለትም። በተዘረፈ የድሆች ድካም ህንፃዎችን ቢገነቡም የራስ ባልሆነ ጌጥ አንኮራም። የወያኔ የሆነ የኛ አይደለም፤ የእነሱ መክበር የኛ መክበር አይደለም። ወያኔ እና የኢትዮጵያ ሕዝብ ገዢና ተገዢ፤ በዳይና ተበዳይ፣ ገፊና ተገፊ ናቸው።
ተበዳይና ተገፊ የሆነው የኢትዮጵያ ሕዝብ በዘረኞች፣ ሙሰኞችና ከፋፋዮች የህወሓት ባለሥልጣኖቻቸውና ሎሌዎቻቸው ላይ ይነሳሉ። የተጀመረው ሕዝባዊ እምቢተኝነት አመቺ በሆኑ መንገዶች ሁሉ ይጧጧፋል።
የወያኔ ትዕዛዛትን መሻር፤ በሥራ ላይ መለገም፤ ግብር አለመክፈል፤ አድማ መምታት፤ የወያኔ ካድሬዎችን ማግለልና ማዋረድ፤ የነፃነት ኃይሎችን መደገፍ፤ የፓሊስና የጦር ሠራዊት አባላትን ማቅረብ እና በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ እነሱም የትግሉ አካል እንዲሆኑ ማበረታታት፤ ህሊና ያላቸው የኢሕአዴግ አባላት የሕዝቡን ትግል እንዲያግዙ ማበረታታት … – እነዚህንና እነዚህን የመሳሰሉ በርካታ የትግል ስልቶች ከአሁን ጀምሮ በተከታታይ በሥራ ላይ መዋል ይኖርባቸዋል። የወያኔን የጭቆና ምሽግ ከውስጥ መሸርሸር፤ ከውጭ መደርመስ ይኖርበታል። የመሸርሸርና የመደርመስ ሥራዎች ተደጋግፈው እንዲሄዱ ማድረግ ይገባል። ጊዜው የእምቢተኝነት ነው።
ግንቦት 7: የፍትህ፣ የዲሞክራሲና የነፃነት ንቅናቄ የኢትዮጵያ ሕዝብ አጠገቡ ባሉት መሪዎቹ አስተባባሪነት በአንድነት እንዲነሳ ጥሪ ያቀርባል፤ በመላው ዓለም ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያዊያንም በኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረገው ሁለገብ ትግል በጽናት እንዲደግፉ ያሳስባል። ይህንን ትግል በድል መወጣት ግዴታችን ነው፤ እንወጣዋለንም!
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!

Monday 10 November 2014

የህወሃቱን ፖለቲካ የአዋጁን በጀሮ!


ህወሃት በተፈጥሮው የፖለቲካ ብዙህነት ወይም ብዝሃነትን ማቻቻል የሚባል ነገር አያውቅም። ሌላው ቀርቶ በራሱ በድርጅቱ ውስጥ የሚነሱ የተለዩ ሃሳቦችን ሁሉ እንደጠላት ሃሳብ ፈርጆ ሰዎችን ደብዛቸውን ማጥፋት የተለመደ የህወሃት አሰራር ነው። ይህን የህወሃት ባህርይ በቅጡ ለመረዳት በቅርቡ የቀድሞው የህወሃት አመራር አባል የነበረው አቶ ገብሩ አስራት የጻፈው መጽሃፍ ጥቂት ገጾች በማየት መረዳት ይቻላል። ተቃዋሚ ፓርቲ ሰላማዊም ሆነ አልሆነ በህወሃት እንደጠላት ነው የሚቆጠረው።
ሰሞኑን ከትግራይ የህዝብና የመንግስት ግንኙነት ቢሮ ከሚባለው መስሪያ ቤት በትግረኛ ተጽፎ ለአባለት በሚስጥር የተሰራጨ ደብዳቤ ማንኛውምንም ተቃዋሚና ከህወሃት ውጭ የሚያስብና ህወሃትን የማይከተል ሁሉ “ፀላኢቲ” ጠላቶች ሲል ይፈርጃል። በዚህ ባለ 5 ገጽ ደብዳቤ ውስጥ እነዚህን “ፀላኢቲ” እንዴት እንደሚያሳድዱ፣ እንዴት እንደሚያዋክቡና እንደሚያጠፉ የሚመክር መመሪያ የሚሰጡ ሃሳቦች ተቀምጠዋል። በደብዳቤው ላይ ከአናቱ ሆነው የሚያስተዳደሩትን ወገናቸውን እንኳን አይለይም። በአጭሩ እኛ እንዳንመርጥ የሚፈልግ፣ የሚቀናቀንና ሌሎች ሰላማዊ ፓርቲወችን የሚመራና የሚደግፍ ሁሉ ፀላኢቲ ነው።
ይህ ለ2007 ዓ.ም የክትትል ስራ የተመደበው የህወሃት ቡድን ስራውን የሚያከናውነው ከታክስ ከፋዩ በሚገኝ የመንግስት ገንዘብ መሆኑ ይታወቃል።
ዘንድሮ የምርጫ አመት መሆኑን ተከትሎ የፀላኢቲ ክትትልና አፈና ከአሁን ተጠናክሮ በመካሄድ ላይ መሆኑም እየታየ ነው። ጠንካራ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች፣ ጋዜጠኞች፣ በየክልሉ ያሉ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎችን ሁሉ በመታፈንና ወህኒ በመውረድ ላይ ናቸው።
የህወሃት ኢህአዴግ መሪዎች በአለም ዙሪያ ነጻነቴን የሚል የህዝብ ድምጽ በሰሙ ቁጥር የሚሰማቸውን ድንጋጤ የሚቀንሱት ዜጎችን በማፈን፣ በመግደል፣ በማሰቃየትና በማሰር ብቻ ነው።
ለህወሃት ምርጫና መድብለ ፓርቲ መልክን አሳምሮ ተቀባይነት ወደ ምእራባውያን ለልመና ለመውጫ እምጅ ዴሞክራሲያዊ ምርጫና የህዝብ ልእልና የሚባል ነገር ባጠገባቸው እንዲያልፍ ስለሚፈልጉ የሚያደርጉት አለመሆኑን በብዙ መንገዶች አሳይተውናል።
ከህወሃት ውጭ ያልህ የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ አንተ ለወያኔ/ህወሃት ፀላኢቲ ጠላት ነህ። ወገኖቼ ብለህ የምታስብ ሁሉ ይህን የሚስጥር ደብዳቤያቸውን በማየት ብቻ ሳይሆን በተግባር አይተሃልና።
ያለህ ምርጫ እንደአባቶችህ፡-
እልም እንጅ ውሃ አይላመጥም፣
ጠላት ወዳጅ ላይሆን አልለማመጥም።
ብለህ መነሳይ ይኖርብሃል።
ትእግስት፣ አስተዋይነትና የፍቅር መንገድ መመኘት ከህወሃት ፀላኢቲነት አያላቅቅም። ህወሃትን ማስወገድ በጠላትነት ፈርጆ ሊውጥህ የመጣ ጠላትን ማስወገድ ማለት ነው።
ግንቦት 7 የፍትህ፣ የነጻነትና የዴሞክራሲ ንቅናቄ ከዚህ በጠላትነት ከፈረጀህ የዘርፎ አደሮች ቡድን እንድትላቀቅ አቅሙን በመገንባት ለወሳኝ ፍልሚያ እተዘጋጀ ነው። መላው ወገናችን ወያኔ የፈጠረልህን የክፍፍልና የልዩነት አጥር እያፈራረስክ አንድነትን አጠንክር። በያለህበት ለነጻነትህ ተነሳ። ኑሮን ለማሸነፍም ሆነ መረጃ በማጣት በወያኔ ስር ተደራጅተህ በሎሌነት እንድታገለግል የተፈረደብህ ወገን ሁሉ ወያኔ ጠላት ብሎ እንደሚቆጥርህ አትዘንጋ። የነፃነታችን ቀን ቅርብ ነው።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!