Tuesday 23 December 2014

ሞትን ሸሽቶ ተራ ሞት ከመሞት ከገዳዮች ጋር ተፋልሞ በክብር መሞት ኢትዮጵያዊነት ነዉ



ወጣቱ ትዉልድ በየትኛዉም አገር ወይም ህብረተሰብ ዉስጥ በአገር ልማት’፤ በመሰረታዊ ተቋሞች ግንባታና አገርን በመከላከል ስራዎች ላይ የተሸከመዉ ኃላፊነት ከሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች የበለጠ ነዉ። እንደ ኢትዮጵያ አይነት ዘረኛ አምባገነኖች በነገሱበት አገር ደግሞ ከላይ ከተጠቀሱት አገራዊ አደራና ሀላፊነቶች በተጨማሪ ወጣቱ ትዉልድ እራሱንና ወገኖቹን ከዘረተኝነትና ከአምባገነንነት አላቅቆ በእኩልነት ላይ የተመሰረተ ዲሞክራሲያዊ ስርዐት የመገነባት ተጨማሪ ሀላፊነት አለበት። ወጣቱ ትዉልድ የኢትዮጵያን አገራዊ ራዕይ የተሸከመ ደከመኝን የማያዉቅ ተከታታይነት ያለዉ የማይነጥፍ የህይወት ምንጭ ነዉ። በእርግጥም ወጣትነት የህይወት ህልምና ፊቺዉ አብረዉ የሚገለጹበት የእድሜ ክልል ነዉ። ወጣቱ ደግሞ ራዕይ ተሸካሚ ብቻ ሳይሆን የተሸከመዉን ራዕይ እዉን ሆኖ ለማየትና ለማሳየት ብቃቱ፤ ችሎታዉና ፍላጎቱ ያለዉ መበአካሉም በመንፈሱን ጠንካራ የሆነ የህብረተሰብ ክፍል ነዉ።
አገራችን ኢትዮጵያ በአለም ታሪክ ዉስጥ እንደ አገር ተመዝግባ በኖረችባቸዉ ረጂም አመታት ዉስጥ የየዘመኑ ወጣት ለእናት አገሩ ሠላም፤ ብልጽግናና የግዛት አንድነት መከበር ይህ ነዉ ተብሎ በቃላት ሊነገር የማይችል ትልቅ መስዋዕትነት ከፍሏል ዛሬም እየከፈለ ነዉ። ትናንት በአባቶቻችን ዘመን የአገራቸዉን ዳር ድንበር በጠላት አናስደፍርም ብለዉ ጫካዉንና ዱሩን ቤታቸዉ ያደረጉ በላይ ዘለቀን፤ አብዲሳ አጋንና ጃገማ ኬሎን የመሳሰሉ ወጣቶች ነበሩን። በ1970ዎቹ ደግሞ ሰዉ በላዉን የደርግ ስርዐት ፊት ለፊት ተጋፍጠዉ ለእናት አገራቸዉ ኢትዮጵያ የህይወት መስዋዕትነት የከፈሉ በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶች ነበሩ። ዛሬም ዘረኛዉን የወያኔ ስርዐት ለማስወገድና አገራቸዉ ኢትዮጵያን የእኩሎች አገር ለማድረግ በየቀኑ የአካልና የሕይወት መስዋዕትነት የሚከፍሉ ኢትዮጵያዉያን ወጣቶች ቁጥር በቀላሉ የሚገመት አይደለም። ለምሳሌ በ1997 ዓም የህዝብ ድምጽ ይከበር ብለዉ በሰላማዊ መንገድ ጥያቄ ያቀረቡ ከሁለት መቶ በላይ ወጣቶች የጦር ሜዳ መሳሪያ ከታጠቁ አግዓዚ ነብሰ ገዳዮች ጋር ባዶ እጃቸዉን ተጋፍጠዉ በክብር ተሰዉተዋል።
ከላይ ከፍ ሲል አጽንኦት ሰጠተን እንደገለጽነዉ ወጣቱ ትዉልድ የህብረተሰብ አንቀሳቃሽ ሞተር ነዉ። ሀኖም ሞተር ከራሱ ዉጭ ሌሎችን ማንቀሳቀስ የሚችለዉ መጀመሪያ እሱ እራሱ መንቀሳቀስ ሲችል ነዉ። የኢትዮጵያም ሆነ የማንኛዉም አገር ወጣት ሞተር ሆኖ የሚኖርበትን ህብረተሰብ ማንቀሳቀስ እንዲችል ከፍተኛ የመንግስትና የሁሉም ህብረተሰብ ያላሰለሰ ድጋፍ ያስፈልገዋል። ከሁሉም በላይ ደግሞ ወጣቱ በነጻነት መንቀሳቀስ የሚችልበት የፖለቲካ፤የማህበራዊና ኤኮኖሚያዊ ድባብ ያስፈልገዋል። እዚህ ላይ አንድ እጅግ በጣም የሚያሳዝነንና የሚያሳስበን ጉዳይ አለ፤ እሱም የኢትዮጵያ ወጣት የእድገት ሞተር ሆኖ አገሩን የሚያንቀሳቅስበት ቀርቶ እሱ እራሱም የነጻነት አየር የተነፈሰበት አንድም የታሪክ አጋጣሚ የለም። በተለይ በወያኔ ስርዐት ዉስጥ ከልጅነት ወደ ወጣትነት የተሸጋገረዉ ኢትዮጵያዊ ሁሉ አገር፤ አንድነትና ኢትዮጵያዊነት ከሚባሉ ትልላቅ ብሄራዊ እሴቶች ጋር እንዳይተዋወቅ ተደርጎ ያደገ ወጣት ነዉ።
የዛሬዉ ዘመን ኢትዮጵያዊ ወጣት በጻፈ ቁጥር የሚደበደብ፤ ባነበበ ቁጥር የሚጋዝ፤ ተናግሮ ሀሳቡን በገለጸ ቁጥር ደግሞ ከየመንገዱ እየተለቀመ የት እንደደረሰ እንኳን ሳይታወቅ ደብዛዉ የሚጠፋ ቀን የጨለመበት ወጣት ነዉ። ባጠቃላይ ወያኔ ስልጣን ይዞ በቆየባቸዉ ባለፉት ሃያ ሦስት አመታት ዉስጥ የኢትዮጵያ ወጣት የአባቶቹን ታሪክ እንዳያዉቅና ከዘመናዊ የመረጃ ቴክኖሎጂ ጋር ሳይተዋወቅ ድቅድቅ ጨለማ ዉስጥ እንዲኖር ተደርጓል። የኢትዮጵያ ወጣት ከመረጃ ቴክኖሎጂ ጋር ተዋዉቆ እራሱን ካደራጀና ከጓደኞቹ ጋር ባሰኘዉ ግዜ ሁሉ ከተገናኘ በአገሩ የፖለተካና ማህበራዊ መድረኮች ላይ የሚጫወተዉን ሚና ወያኔ ስለሚረዳ የስልጣን ዘመኑን ለማራዘም ከወሰዳቸዉ እርምጃዎች አንዱና ዋነኛዉ ወጣቱ ህብረተሰብ ከመረጃ ቴክኖሎጂ ጋር ያለዉን የቅርብ ግኑኝነት መስበር ነዉ። ይህ ፀረ አገርና ፀረ ዕድገት እርምጃ ደግሞ ወጣቱን ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ አገራችን ኢትዮጵያ በመረጃ ቴክኖሎጂ ዕድገትና ስርጭት የአለማችን የመጨረሻዋ ጭራ አገር እንድትሆን አድርጓታል። ይህ ደግሞ የኢትዮጵያን ወጣት አማራጭ አሳጥቶ ከዚህ ቀደም ታይቶም ተሰምቶም በማያዉቅ ፍጥነትና ብዛት አገሩን እየጣለ እንዲሰደድ አድርጎታል።
የተባበሩት መንግስታት ድርጅትና ሌሎችም አለም አቀፍና አህጉራዊ ድርጅቶች ያደረጉት ጥናት በግልጽ እንደሚያመለክተዉ ምሁሩና ወጣቱ ትዉልድ በከፍተኛ ቁጥር ከሚሰደድባቸዉ አገሮች ዉስጥ ኢትዮጵያ በዓለዉ ዉስጥ ቀዳሚዉን ቦታ የያዘች አገር ናት። ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች የኢትዮጵያን አኮኖሚ የአፍሪካ የዕድገት ምልክት አድርገነዋል እያሉ ቢፏልሉም ይህ አሳደግነዉ የሚሉት ኤኮኖሚ ስራ አልባ ኤኮኖሚ በመሆኑ የራሱን አገር መገንባት የነበረበት ኢትዮጵያዊ ወጣት ወንድ ሴት ሳይል እጅግ በጣም በሚያስፈራ ፍጥነት አገሩን እየለቀቀ በመዉጣት ላይ ነዉ።
ዛሬ በዘለም ዙሪያ ከደቡብ ኮሪያ እስከ አዉስትራሊያ፤ ከሳዑዲ አረቢያ እስከ ካናዳ በየአህጉሩ፤ በየአገሩና በየደሴቱ ላይ ኢትዮጵያዉያን ስደተኞች የሌሉበት አገር የለም። በ1970ዎቹ መጀመሪያ አካባቢ የደርግን ጭፍጨፋ እየሸሸ ከአገሩ መሰደድ የጀመረዉ ኢትዮጵያዊ ወጣት ዛሬም ከ37 አመታት በኋላ ኢትዮጵያ ዉስጥ ያለዉ አገዛዝ የለየለት ነብሰ ገዳይ አገፈዛዝ በመሆኑ የኢትዮጵያ ወጣት አሁንም አገሩን እየለቀቀ በመዉጣት ላይ ነዉ። የስደት ጉዞ ብርድና ቁር፤ ሀሩርና ንዳድ፤ እንዲሁም ህመም፤ ቁስልና ሞት የተቀላቀሉት ለወገንም ለባዳም የማይመኙት እጅግ በጣም አደገኛ ጉዞ ነዉ። ስደት ጉዞዉ ብቻ ሳይሆን ስደተኞች በስደት የሚኖሩበት አገርም ቢሆን ለአካልም ለመንፈስም የማይመች ቦታ ነዉ። ሴቶች እህቶቸቻችን በየቀኑ ወደ አረብ አገር የሚጎርፉት አካለቸዉ ላይ የፈላ ዉኃ እንደሚደፋ፤ ከፎቅ ላይ እንደሚወረወሩና በአረብ ጎረምሳ በየቀኑ እንደሚደፈሩ እያወቁ ነዉ ከወያኔ ጋር ከመኖር ስደት ይሻላል ብለዉ አገራቸዉን ለቅቀዉ የሚሰደዱት። ወንዶች ወንድሞፐቻችንም ቢሆኑ የሰሃራን በረሃና የቀይ ባህርን የመከራ ጉዞ ቆርጠዉ የሚገበቡበት ከቀዳዳ ይሻላል ጨምዳዳ ብለዉ ነዉ እንጂ በየበረሃዉና በየባህሩ ላይ እንደወጣ የቀረዉ ኢትዮጵያዊ ቁጥር እጅግ በጣም ብዙ እንደሆነ ሳያዉቁት ቀርተዉ አይለደም። ለመሆኑ ኢትዮጵያዉያን ይህንነ ሁሉ ቸግርና ጣጣ እያወቁ ወነድ፤ሴት፤ ወጣት አዛዉንት፤ ሳራተኛና ገበሬ ሳይል ሁሉም በጅምላ እትብታቸዉ የተቀበረበትን አገር እየለቀቁ የሚሰደዱት ለምንድነዉ?
ኢትዮጵያዉያን የሚሰደዱት ወያኔን እየጠሉ ነዉ ወይም የወየኔ ዘረኝነት፤ ከፋትና ጥላቻ እንገፍግፏቸዉ ነዉ ብለዉ የሚገምቱ ብዙ ኢትዮጵያዉያን ሰዎች ሊኖሩ ይቻላል። በጥቅሉ ሲታይ ግምታቸዉ ትክክለኛ ግምት ነዉ፤ የወያኔ ዘረኝነትና ፀረ ኢትዮጵያ አቋም ብዙ ኢትዮጵዉያንን አንገፍግፏል፤ አበሳጭቷል ወይም አስቆጥቷል። ሆኖም ሰዎች ስለተቆጡና ስለተንገፈገፉ ብቻ እንደ ምፅአት አገራቸዉን እየለቀቁ አይወጡም። ኢትዮጵያዉያን አገራቸዉን እየለቀቁ የሚወጡት ከወያኔ እስር፤ ድብደባና ግድያ ለማምለጥ ነዉ ብለን መገመትም እንችላለን። ትክክለለኛ ግምት ነዉ። ግን ስንቱ ኢትዮጵያዊ ነዉ ኬንያ፤ ማላዊ፤ ሞዛምቢክ፤ ግብፅ’ የመንና ሊቢያ ድረስ ሲንከራተት በየመንገዱ እየሞተ ለቀብር እንኳን የማይበቃዉ? ደግሞም የሰዉ ልጅ ባህሪይ የሚያሳድደዉንና የሚገድለዉን እየገደለ መሞት ነዉ እንጂ ሞትን እየሸሰ ጣረ ሞት ዉስጥ መግባት አይደለም። እዉነቱን ለመናገር የኢትዮጵያ ወጣት አገሩን በገፍ እየለቀቀ የሚሰደደዉ የወያኔ ዘረኞች ተስፋዉን ስለገደሉበትና የወደፊቱን ስላጨለሙበት ነዉ።
ተስፋ የሰዉ ልጆች የመኖር ዋስትና ነዉ። እኛ ሰዎች እየከፋንም ቢሆን ደስ እንዳለዉ ሰዉ የምንኖረዉ ይኖረናል፤ ይመቸናል ወይም ክፉዉ ቀን አልፎ መልካም ቀን ይመጣል በሚል ተስፋ ነዉ።ተስፋ የሞተ ቀን ለምን እንደምንኖር ስለማናዉቅ አገር ጥለን መሰደድ ብቻ ሳይሆን ከዚህም የከፋ ብዙ ነገር ማድረግ እንችላለን። ወያኔ ስልጣን ይዞ የቆየባቸዉን ያለፉት ሓያ ሦስት አመታትን ትተን ከ2000 እስከ 2007 ያሉትን ሰባት አመታት ብቻ ስንመለከት ማላዊ ሀይቅ ወስጥ፤ ሰሃራ በረሃ ዉስጥ፤ ኤደን ባህረ ሰላጠና ባቢኤል መንደብ ዉስጥ እጅግ በጣም ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ኢትዮጵያዊ የአዉሬ ስራት ሆኖ ቀርቷል። ነፃነትና የተሻለ ኑሮ እናገኛለን ብለዉ በኮንቴነር ተጭነዉ ወደ ደቡብ አፍሪካ ይጓዙ የኘበሩ ከ50 በላይ ኢትዮጵያዉያን በእግራቸዉ እየተራመዱ ከገቡበት ኮነቴነር እሬሳቸዉ እየተጎተተ ወጥቷል።
ስደትንና እየተሰደደ ደብዛዉ የሚጠፋዉን ኢትዮጵያዊ በተመለከተ የኢትዮጵያ ህዝብ ብዙ ለጆሮ የሚከብዱ ዜናዎችን ሰምቷል። ባፈዉ ህዳር ወር ማለቂያ ላይ ከወደ የመን የተሰማዉ ዜና ግን ለጆሮ የሚሰቀጥጥ ብቻ ሳይሆን ለምን ኢትዮጵያዊ ሆኜ ተፈጠርኩ የሚያሰኝ ነዉ። አገራቸዉ ኢትዮጵያ ዉስጥ ወያኔ ተስፋቸዉን ያጨለመባቸዉ አያሌ ኢትዮጵያዉያን እንደ ዜጋ የሚመለከታቸዉና የት ገቡ ወይም የት ደረሱ የሚል መንግስት ስለሌላቸዉ ለቀበር እንኳን ሳይበቁ ቀይ ባህር ዉጧቸዉ ቀርቷል። ለወትሮዉ ለኢትዮጵያዉያን ስደተኞች ብዙም ግድ የሌለዉ የየመን መንግስት እንኳን ሰብዓዊነት ቆርቁሮት ቀይ ባህር እንደዋጠ ያስቀራችዉን ኢትዮጵያዉያን አስከሬን ፍለጋ ጀልባና መርከብ ሲያሰማራ፤ 99 በመቶ ኢትዮጵያዉያን መረጡኝ የሚለዉ የወያኔ አገዛዝ ግን የራሱ ዜጎች ሞት የተመቸዉ ይመስል ሰምቶ እንዳልሰማ ተመልካች መሆኑ አልበቃ ብሎት በተላላኪዉ ጠ/ሚኒስተር በኃ/ማሪያም ደሳለኝ አማካይነት ጭራሽ በአለም ዙሪያ የሚገኙ ስደተኞችን ሲዘልፍና ሲያጥላላ ከርሟል። አሜሪካ፤ አዉሮፓና መካከለኛዉ ምስራቅ ዉስጥ በየጋዜጣዉ በየቴሌቪዥኑና በማህበራዉ ሜድያዉ የአንድ ሳምንት የመወያያ አርዕስት ሆኖ የከረመዉ የኢትዮጵያዉያኑ እልቀት አገራቸዉ ኢትዮጵያ ዉስጥ ግን ለይስሙላ እንኳን ስማቸዉ አልተነሳም።
አዎ እኛ ኢትዮጵያዉያን የትም እንኑር የት በህይወታችን ቆመንም ሆነ ሞተን ዜጎቼ ብሎ የሚቆረቆረልንና ለወገንና ለአገር ልጅ የሚደረገዉን ልዩ እንክብካቤ የሚየደርግልን መነሰግስ/ት የለንም። አልፎ አልፎ የወያኔ ባለስልጣኖች አዉሮፓና አሜሪካ ሲመጡ በየኤምባሲዉና በሚስጢር በሚያዙ ሆቴሎች ለዉይይት የሚጋብዙት ታማኝ ሎሌዎቻቸዉንና የአንድ አካባቢ ተወላጅ የሆኑ ሰዎችን ነዉ እንጂ ብዛት ያለዉን ሌላዉን ኢትዮጵያዊ የት ወደቀ ብለዉ እንኳን አይጠይቁም። እንዲያዉም ከቅርብ ግዜ ወዲህ ከጠ/ሚ ኃ/ማሪያም ደሳለኝን ጨምሮ ሁሉም የወያኔ ባለስልጣኖች በዉጭ አገሮች የሚኖረዉን ኢትዮጵያዊ እንደ ባዕድ መመልከና መዝለፍ ጀምረዋል። ይህ ሁሉ የሚያሳየን አገር ዉስጥም ሆነ በዉጭ አገሮች እኛ ኢትዮጵያዉያን ተገናኝተን እርስ በርስ ካልመከርንና ችግሮቻችንን በጋራ እኛዉ ካልፋታን እንደ ዜጋ የሚንከባከብልን ቀርቶ እንደ ሰብዓዊ ፍጡር የሚመለከተንም እንደሌለን ነዉ። ይህንን ደግሞ ባለፈዉ አመት ሳዑዲ አረቢያ ዉስጥ አሁን በቀርቡ ደግሞ የመን ዉስጥ በግልጽ አይተናል። ወገኖፐቻችን የሆኑ ኢትዮጵያዉያን የመን እንገባለን ብለዉ ቀይ ባህር ዉስጥ የአሳ ሲሳይ ሆነዉ ሲቀሩ በጠ/ሚኒስቴርነት ስም የወያኔ ተላላኪ የሆነዉ ኃ/ማሪያም ደሳለኝ ጭራሽ በአለም ዙሪያ የሱን እርግጫ፤ እስርና የጅምላ ግድያ ሸሽተዉ የተሰደዱ ሲትዮጵያዉያንን እጅግ በጣም አስነዋሪና አስጸያፊ በሆነ መለኩ ሲዘልፋቸዉ ተሰምቷል። የሚገርመዉ ባለፈዉ ህዳር ወር ማለቂያ ላይ ቀይ ባህር ዉስጥ ሰጥመዉ ካለቁት ከሰባ በላይ ወገኖቻችን ዉስጥ ገሚሶቹ ባለፈዉ አመት ከሳዑዲ ተባርረዉ ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱና እነ ቴዎድሮስ አድሃኖም ኢትዮጵያ ለዜጎቿ የማታደርጉወ ምንም ነገር የለም ብለዉ የተናገሩላቸዉ ሰዎች ናቸዉ።
ባጠቃላይ እኛ ኢትዮጵያዉያን አገራችን ዉስጥ ተዋርደናል፤ በስደት በምንኖርባቸዉ አገሮች ዉስጥም ተዋርደናል። አገር ዉስጥ ወያኔ እንዳሻዉ ያስረናል፤ ይደበድበናል ይገድለናል። ይህንን ጠልተን ከአገራችን ስንሰደድ ደግሞ በየበረሃዉና በየባህሩ ላይ ክብርና ወግ ላለዉ ቀብር እንኳን ሳንበቃ እንደወጣን እንቀራል። ካሁን በኋላ እንደ ህዝብ መብታችንና ነጻነታችን ተከብሮ አንደ አገር ደግሞ አንድነታችንና ዳር ድንበራችን ተጠብቆ ለመኖር የምንፈልግ ከሆነ አማራጩ አገራችንን አንደ ምጽዐት ለቅቀን መዉጣት ሳይሆን ለዚህ ሁሉ ዉርደትና መከራ ከዳረጉን ዘረኞች ጋር ፊት ለፊት መግጠምና ይለየለት ማለት ብቻ ነዉ። ወያኔ የሚፈጽምብን ሰቆቃ እንዲቆም፤ አስርና ግድያዉ አክትሞ ስደት እንዲያበቃ ብቸኛዉ አማራጭ እነዚህ ነገሮች ሲፈጸሙ መግለጫ ማዉጣትና ከንፈር መምጠጥ ብቻ ሳይሆን የችግሮቻችንን ምንጭ ማድረቅ ነዉ፤ ወይም ዘረኛዉን የወያኔ አገዛዝና እሱ የገነባዉን ዘረኛ ስርዐት ነቃቅለን ማስወገድ ብቻ ነዉ። በዜግነታችን ተከብረንና በገዛ አገራችን ኮርተን መኖር የምንችለዉ ይህንን ስናደርግ ብቻ ነዉ።

Friday 19 December 2014

የፈሪ ዱላ ነፃነትን አያስቀርም !


!

ህወሃቶች ኢትዮጵያን “ለመምራት” ያላቸው አቅም ተሟጦ አልቋል። ፍርሃት አቅላቸውን አስቷቸዋል። ፍርሃታቸው ጭካኔን ወልዷል። ይህ ጭካኔያቸው ወሰን አጥቷል። ልጥ ባዩ ግዜ እባብ እየመሰላቸው ልጡን በቆመጥ ሲደበድቡ ውለው ያድራሉ። ፍርሃት ያ ደካማ ማሰቢያቸውን ጥርቅም አድርጎ ዘግቶታል። የፈሪ ዓይን ማየት እንደማይችል፤ ጆሮውም መስማት እንደተሳነው ከህወሃቶች ተርድተናል።
እኛ ግን እንዲህ እንላለን ህወሃቶች ዓይናችው እያየ፤ ጆሮዋቸውም እየሰማ የኢትዮጵያ ህዝብ ነፃነቱን ይቀዳጃል። እውነት እውነት እንላችኋለን የነፃነቱ ግዜ እሩቅ አይደለም። ህወሃቶች ከነፍርሃታቸው ወደ መረጡት መቃብራቸው መውረዳቸው እንደማይቀር ቅንጣት ታክል ጥርጣሬ የለንም።
የኢትዮጵያ ህዝብ ምርጫ ነፃነት ነው።ይህን ነፃነት ከህወሃቶች እጅ ለምነን የምናገኘው አይደለም። ነፃነታችንን ታግለንና አሸነፈን የምንቀዳጀው ንፁህ ሃብታችን ነው። ይህን ንፁህ ሃብታችንን በቀማኞች አስነጥቀን ዝም ብንል እርግማን ይሁንብን ያሉ ኢትዮጵያዊያን እያደረጉ ያሉት ትግል ተስፋ ሰጪ ነው። በተለይም ወጣቶች እምቢ ለክብሬ፤ እምቢ ለነፃነቴ እምቢ ለማያውቁን ህወሃቶች ማለታቸውን ስናይ ተስፋችን ከመቸውም ግዜ በላይ ለምልሟል።
ህወሃቶች ኃላፊነት የሚሰማቸው ቢሆኑ ኑሮ “በሃሳባችሁ ባንስማም ልዩነታችሁን መግለፅ የምትችሉበትን መብት ለማስከበር እሰከ ሞት ድረስ እንቆማለን” ይሉ ነበር። አለመታደል ሁኖ ህወሃቶች አገር፤ ህዝብ፤ ወገን የሚባል ቋንቋ በውስጣቸው የለም። ኢትዮጵያም አገራቸው አትመስላቸውም፤ ህዝቡም ወገናቸው እንደሆነ አይሰማቸውም። ህወሃቶች በወንድምና እህቶቻቸው አጥንት ላይ ቁመው ለኢትዮጵያና ለህዝቧ ጠላት መሆንን መርጠዋል። ለነፃነት ብለው በትግል ሜዳ የተሰው ጓዶቻቸውን ሞትም ከንቱ ሞት አድርገው አስቀርተውታል። ይሄ እርግማን ነው።ይሄ እርግማን ደግሞ አሁን ባሉት ህወሃቶች ብቻ የሚቆም ሳይሆን ወደ ልጅ ልጆቻቸው እንደሚሸጋገር ህወሃቶች ለማሰብ አቅቷቸዋል።
ህወሃት የስለጠነ ፖለቲካ አያውቅም። የነፃነትንም ትርጉም ሳያውቅ ነፃ አውጪ ነኝ ይላል። በአገሪቷ ጫንቃ ላይ መቆየት ብቻ የህልውናየ መሠረት ነው ብሎ ካመነም ቆይቷል። ይህን የህልውናየን መሠረት የሚነካ ሁኔታ ከተፈጠረም ጠመንጃየ መመኪያ ጉልበቴ ነው የሚል የማይናወፅ አቋምም ይዟል። ይህ አቋሙ አገሪቷ ከተጋረጡባት አደጋዎች መካከል አንዱ ሁኖ ይታየናል። የዚህ አቋም መዘዙ አሁን ባለው ትውልድ ብቻ የሚያበቃ አይደለም። ወደ ቀጣዩ ትውልድ ተሸጋግሮ የአገሪቷ ዜጎች በሠላም አብረው የሚኖሩበትን እድል እንደሚያበላሸው ህወሃቶች አያውቁም ማለት አይቻልም። ተደጋግሞ እንደተነገረው በህወሃቶች ዘንድ ትውልድ የሚባል ቋንቋ እንዲጠፋ በመደረጉ ለመጪው ትውልድ የሚተርፍ ቂም ትተው ለማለፍ ሳያቅማሙ እየሰሩ ይገኛሉ።
የኢኮኖሚ መዋቅሩ በእነርሱ ብቻ መያዙ ነገ ለእነርሱ ልጆች የደም እንጀራን እንደሚያተርፍላቸው እንዲገነዘቡ ማድረግ ተገቢ ይመስለናል።በህወሃቶች አስተሳሰብ ሌላውን የኢትዮጵያ ህዝብ ድሃ አድርገን ከያዝነው ከዕለት ጉርሱ አልፎ ሂዶ ነፃነትን ይጠይቀናል ለነፃነት የሚከፍለውንም ዋጋ ለመክፈል አቅም አይኖረውም የሚል ሙት ፍልስፍና መመሪያቸው ሁኗል። እኛ ብቻ በኢኮኖሚ ጎልበትን ሌሎቹን የእኛ ጥገኛ ካደረግን ለዘላለም ከነ ልጅ ልጆቻችን ነግሰን እንኖራለን የሚል ቅዥት ውስጥ ሁነው አገሪቷን ወደ ትርምስ እየወሰዷት እንደሆነ እያየነው ነው።ህወሃቶች ከእህል ውሃ የዘለለ ራዕይ እንደሌላቸው የሚታወቅ ነው። ራዕይ አልባዎች ተደራጅተው አገር መምራት ሲጀምሩ አገሪቷና ህዝቧ በሙሉ ራዕይ አልባ ይሆናሉ። መፅሃፍ እንደሚነግረን ደግሞ “ራዕይ አልባ አገር ይጠፋል” ይላል። የህወሃቶች ምኞት ይሄው ነው። እኛ ከሌለን ኢትዮጵያ አትኖርም የሚል ክፉ ምኞት።
ኢትዮጵያዊያን ሆይ !
ህወሃት የጭለማን መንገድ መርጧል። ይሄ መንገዱም አገሪቷንና ህዝቧን ወደ መቀመቅ እየጨመራት ነው። አገሪቷን አስይዞ ከግል ኩባንያዎች ብድር እስከ መለመን ደርሷል። ቀጣዩ ትውልድ ከሚወርሰው ቂምና በቀል በተጨማሪ በእዳ የተያዘ ትውልድ ይሆናል። በቀላል አነጋገር ትውልዱ የባዕድ ተገዢ እንዲሆን ተፈርዶበታል። ህወሃቶች ለመጪው ትውልድ የሚሰጡት ስጦታ ባርነትን እንዲሁም ቂምና በቀልን እንጂ ነፃነትንና አብሮ መኖርን አይደለም።
እንግዲህ ህወሃቶችን አደብ ማስያዝ የዚህ ትውልዱ ግዴታ ይሆናል። ህወሃት ከኢትዮጵያ ፖለቲካ ውሳኔ ሰጪነት ካልተወገደ በቀር በኢትዮጵያ መረጋጋት አይኖርም። ችጋርም አይጠፋም። የንፁህ ሰው ደም ከመፍሰስ አይቆምም። አገሪቷም በእዳ ላይ እዳ ከመጨመር አትመለስም።
ይህ ሁኔታ መቆም እንደሚኖርበት አሁን ሁሉም ተገንዝቧል። ይህ ሁኔታ ግን እንዲሁ በከንቱ የሚቆም አይሆንም። ለዚህ የሚከፈል የደም መሥዋዕትነት የግድ ሁኖብናል። ፍትህ፤ እኩልነት እና ነፃነት የደም ውጤቶች ናቸው። ያለ መሠዋዕትነት የሚመሠረት ፍትህ አይኖርም፤እኩልነትም ቢሆን የብዙዎችን መስዋዕትነት ይጠይቃል፤ የነፃነት ቀንዲል የሚለኮሰው በደም አቀጣጣይነት ነው። ህወሃቶች መሽቶ በነጋ ቁጥር የንፁህ ደም ያፈሳሉ። ዝም ያሉትም ሞት አልቀረላቸውም፤ የተናገሩትም የውርደት የሞት ፅዋቸውን እየተጎነጩ ነው፤ ሌሎቹም ከሞት በባሰ ሁኔታ በየማጎሪያ ቤቱ የመከራ ፅዋቸውን እየተጋቱ ነው። ይሄ የውርደት ታሪክ መቀየር ይኖርበታል።
የሠማያዊ ፓርቲ ፅ/ቤት ጥበቃ ሠራተኛ የ72 ዓመቱ አቶ ቀኖ አባጆቢርን ለእስር የዳረገ አገዛዝ ነው ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው።የ72 ዓመት ኢትዮጵያዊ ሽማግሌን አንኳ የሚፈራ ቡድን ነው አገሪቷን የተቆጣጠራት። አቶ ቀኖ የእለት ጉርሳቸውን ለመሸፈን ደመወዝ ተቆርጦላቸው የጥበቃ ሥራ የሚሰሩ እንጂ የፓሪት አባል አልነበሩም ሆኖም ግን ታፍነው ለእስር ተዳርገዋል። የህወሃቶች ግፍ ማብቂያ እና ወሰን አጥቷል።እነዚህ ቡድኖች እየፈፀሙ ያሉት ግፍ ጥላቻን እየወለደ፤ ቂምን እየተከለ ቀጥሏል። የህዝቡ ቂም እንደ ተዳፈነ እሳት የሚቀጣጠልበትን ግዜ እየጠበቀ ነው።ይህ ግዜ የመጣ ቀን ህወሃቶች እና አሸከሮቻቸው ወየውላቸው።ያ ግዜ ደግሞ ያለ ጥርጥር በእርግጠኝነት ይመጣል።ፈጥኖ እንዲመጣ በእኛ በኩል የሚቻለንን ሁሉ እያደረግን ነው።
ከህወቶች በተጨማሪ በዚያች አገር ታሪክ ውስጥ ፌዴራል ፖሊስ ተብለው የተደራጁት እና ከሰው መፈጠራቸውን የረሱ ቡድኖች መኖር በብርቱ ያሳስበናል። የፌዴራል ፖሊስ አባላት እየፈፀሙ ያሉት ጭካኔ አስገራሚ ነው። የዝህ ጦር አባላት ሰው ሁነው መፈጠራቸውን እስክንጠራጠር ድረስ አስገርመውናል። እንግዲህ የፌዴራል ፖሊስ አባላት ብዙ ግዜ ማሳሰቢያ ልከንላችኋል። አሁንም በተጨማሪ እንነግራችኋለን። ነገራችንንም ለታሪክ ይቆይ ዘንድ በመዝገብ እናኖረዋለን። አሁን የጭካኔ ሰይፋቸሁን መዛችሁ እንደ ፈለጋችሁ የምትገሏቸው ዜጎች ወገኖቻችሁ መሆናችሁን አትርሱ። ነገ ቢርባችሁ የሚያበሏችሁ፤ ብትወድቁ የሚያንሷችሁ፤ ብትጠሙ የሚያጠጧችሁ ዛሬ በያዛችሁት ጠመንጃ የምትገድሏችው ወገኖች ናቸው። እናንተ ግን ይሄን እውነት ለማየት አዚም የተደረገባችሁ ይመስላል።
ፌዴራል ፖሊሶች ታዝዤ ገደልኩ በማለት የምታመልጡ እንዳይመስላችሁ። ታዝዤ ገደልኩ ማለት ሥራየ መግደል ነው ማለት ነው። ሥራው መግደል የሆነ ማንም ይሁን ማን ወንጀለኛ ነው። ወንጀለኛ ደግሞ ተመጣጣኝ የሆነ ቅጣት መቀጣቱ አይቀርም። ስለሆነም የፌዴራል ፖሊስ አባላት በሰላማዊ መንገድ ኑሮ ተወወደብኝ የሚለውን ወንድማችሁን በቆመጥ ደብድቡ ስትባሉ አይ ሠላማዊ ሰውን እጠበቅ ዘንድ እንጂ እደበድብ ዘንድ ህግ አይፈቅድልኝም ማለት ስትችሉ ያገኛችሁትን ሁሉ እየሰበራችሁ መኖራችሁን እያየነው ነው። ይሄ በምንም መሥፈርት ትክክል አይደለም። አንዱ ታዝዤ ወንድምህን ወይም ልጅህን ወይም ደግሞ አባትህን ገደልኩ ቢልህ ምንድ ነው የሚሰማህ? መቸስ ታዘህ ነው እንግዲህ ምን ይደረጋል እንደማትል እርግጠኞች ነን። እኛ ሁላችን አንተ የፌዴራል ፖሊስ አባል በምትፈፅመው ጭካኔ በእጅጉ ተጎድተናል።የያዘከው ጠመንጃ የሸንበቆ ምርኩዝ የሚሆንበት ግዜ ወደ አንተ ፈጥኖ እየመጣ ነው። አሁን የያዝከው ቆመጥ ተሰብሮ ይወጋሃል በተወጋህ ግዜ ግን ዞር መግቢያ እንዳታጣ ለራስህ ተጠንቀቅ። አዛዦችህ እንደሆነ የአገሪቷን ንብረት ዘርፈው ወደ ውጭ አገር አሽሽተዋል፤ የቀረውንም በዘመድ አዝማዶቻቸው ሥም ብዙ ህንፃዎችን አሰርተው እየተዘባነኑበት ነው። አንተ ግን ከቀሪው ወገንህ ጋር ደም ትቃባለህ። ነገ ሌላ የተለየ አዲስ ቀን ነው። አዲስ ቀን በሆነ ግዜ መግቢያ እንዳታጣ አሁኑኑ ራስህን ከዘረኞች፤ ከዘራፊዎችና ከግፈኞች ጎን አግልለህ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጎን እንድትሰለፍ ደግመን ደጋግመን እንመክርሃለን። ይሄን ምክር አልስማ ካልክ ግን የሚመክርህ መከራ በደጅህ ፈጥኖ ይመጣል።
በመጨረሻም ህወሃቶችን ለማስወገድ የሚደረገው ትግል ተፈፍሞ መቀጠል የኖርበታል። ሁሉም በሚችለውና በሚያምነበት መንገድ ሳያቅማማ ይታገል። በሁሉም መንገድ የሚደረገው ትግል ፍሬ አፍርቶ በነፃነት እንደሚቋጭ ባለ ሙሉ ተስፋ ነን። እኛ የጀመርነውን ሁለ-ገብ ትግል አጠናክረን ተያይዘነዋል። ዕለት ዕለት እየጎለበትን እየሄድን ነው። አደረጃጀታችንም መሠረት ይዟል። ካሁን ወዲያ ትግላችንን የሚያቆም ምድራዊ ኃይል የለም። ነፃነታችንን ሳንቀዳጀ የጀመርነውን ትግል አናቆምም።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !

Tuesday 9 December 2014

ብሄራዊ ብድር የዕድገታችን ምንጭ እንጂ የደኅንነታችን ስጋት ሊሆን አይገባም


እኛ ሰዎች ሁሌም ከምንፈራዉና ከምንጠላዉ አንዴ ከገባንበት ደግሞ የቱንም ያክል ብንጠላዉና ብንፈራዉ እየደጋገምን የምንዘፈቅበትና በቀላሉ የማንወጣዉ አዘቅት ቢኖር ብድር ወይም የብድር ልጅ የሆነዉ ዕዳ ነዉ። ብድር ግለሰቦች ብቻ ሳይሆኑ የንግድ ድርጅቶች፤ ማዘጋጃ ቤቶች፤ ትላልቅ ኮርፓሬሺኖችና አገሮች በአጭርና በሪጂም ግዜ የሚያጋጥማቸዉን የገንዘብ እጥረት የሚሸፍኑበት መንገድ ነዉ። ወይም ቀለል ባለ አማርኛ ብድር ወደፊት በምናገኘዉ ገቢ ዛሬን መኖር ማለት ነዉ። ብድር ግለሰቦች፤ ድርጅቶች ወይም አገሮች የመከፈል አቅማቸዉን እያዩ ቢበደሩና የተበደሩትን ገንዝብ ዉጤታማ በሆነ መንገድ ከተጠቀሙበት የእድገትና የብልጽግና መንገድ የሚከፍት አለዚያም የምንበደረዉ ብድር ከአቅም በላይ ከሆነና ዉጤታማ ባልሆነ መልኩ ከተጠቀምንበት ደግሞ በቀላሉ የማንወጣዉ መቀመቅ ዉስጥ ይዞን የሚገባና ጫናዉ ከትዉልድ ወደ ትዉልድ የሚተላለፍ ዕዳ ነዉ። ዕዳ ደግሞ በተለይ አገሮች የሚገቡበት ዕዳ ተከፍሎ ካላለቀ ወይም በምህረት ካልተሻረ በቀር ወለዱ ወለድ እየወለደ በተበዳሪ አገሮች የኤኮኖሚ እድገት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ የሚያደርግ የዕድገትና የብልፅግና ጠላት ነዉ። ዛሬ ሰፋ አድርገን የምንመለከተዉ ብድርና ዕዳን ቢሆንም ዋናዉ ትኩረታችን ግን አገራችን ኢትዮጵያን ጨምሮ በታዳጊ አገሮች የኤኮኖሚ ዕድገት ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ የሚያደርገዉን ብሄራዊ ብድርና ዕዳ ነዉ። ሁላችንም እንደምናዉቀዉ አገራችን ኢትዮጵያ ባለፉት ሃያ አመታት በብድር ላይ ብድር እየተበደረች አንዱንም ሳትከፍል በድጋሚ እየተበደረች ከድጡ ወደማጡ እየገባች ነዉ።
የኢትዮጵያ መንግስት መንግስታዊና መንግስታዊ ካልሆኑ የዉጭ አገር ምንጮች ብድር መበደር ከጀመረ ብዙ አመታት ተቆጥረዋል።ከቀዳማዊ ሚኒልክ በኋላ ኢትዮጵያን ለረጂም አመታት የመሩት ሦስቱ መንግስታት የብድር ጥማት ከፍተኛ ቢሆንም በብድር መጠኑም ሆነ በተከማቸ የዕዳ መጠኑ ዛሬ በስልጣን ላይ አንዳለዉ እንደ ወያኔ አገዛዝ የአገራችንን ብሄራዊ ደህንነት ለአደጋ ባጋለጠ መልኩ ብድር የተበደረና ዕዳ ዉስጥ የተዘፈቀ አገዛዝ ኢትዮጵያ አይታ አታዉቅም። የወያኔ አገዛዝ አገር ዉስጥ ቦንድ እየሸጠና ብሔራዊ ባንክን እያስገደ በተለያየ መልኩ የሚወስደዉ ብድር ከአለም ባንክ፤ ከአለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት፤ ከዉጭ አገር ባንኮችና አበዳሪ አገሮች በየአመቱ ከሚበደረዉ ብድር ጋር ተደምሮ የዛሬዉን ኢትዮጵያዊ ብቻ ሳይሆን የዛሬዉን ኢትዮጵያዊ የልጅ ልጆች ጭምር ባለዕዳ አድርጓቸዋል።
የወያኔ አገዛዝ ለህዳሴዉ ግድብና ለእድገትና ትራንስፎርሜሺን ዕቅድ ማስፈጸሚያ በሚል የአገሪቱን አመታዊ ገቢና የመክፈል አቅም በላገናዘበ መልኩ እጅግ በጣም ከፍተኛ ቁጥር ያለዉ ገንዝብ ከተለያዩ የአገር ዉስጥና የዉጭ አገር ምንጮች እየተበደረ ነዉ። ይህ መጠነ ሰፊ ብድር በረጂም አመት የሚከፈልና ከፍተኛ ወለድ የተሸከመ ሲሆን ወያኔ ይህ ብዙ ኢትዮጵያዉያንን ያሰጨነቀ ብሄራዊ ዕዳ አልበቃ ብሎት ከአቅም ዉጭ የጀመራቸዉን ፕሮጀክቶች ለማስጨረስ ነዉ በሚል ሰበብ አሁንም አገራችን ኢትዮጵያን ከዕዳ ወደ ዕዳ እየከተታት ይገኛል። በተለይ ወያኔ አበዳሪ አገሮች፤ የአለም ባንክና ወዳጆቹ የሆኑ መንግስታት ጭምር ተዉ ይቅርብህ ብለዉ እየመከሩት አልሰማ ብሎ በዚህ አመት ለመሸጥ ያሰበዉ ሉዓላዊ ቦንድ ወይም ፈረንጆቹ ሶቨርን ቦንድ ብለዉ የሚጠሩት ቦንድ ሽያጭ የጉዳዩ አሳሳቢነት የገባቸዉን ኢትዮጵያዉያንንና የኢትዮጵያ ወዳጆች ከወዲሁ እያሰጨነቀ ነዉ። በእርግጥም ሉዓላዊ ቦንድ ሽያጭ የሚያስጨንቅ ብቻ ሳይሆን አንደ ኢትዮጵያ አይነቶቹን ቀድሞዉኑም ዕዳ ዉስጥ የተዘፈቁ ደሃ አገሮች ህልዉና አደጋ ዉስጥ የሚከት የኤኮኖሚ ዕድገትን ብቻ ሳይሆን የአገር ደህንነትን ጭምር የሚፈታተን አደገኛ ጅምር ነዉ። ለመሆኑ ሉዓላዊ ቦንድ ምንድነዉ? አደገኛነቱስ ምኑ ላይ ነዉ?
ሉዓላዊ ቦንድ አገራቸዉ ዉስጥ ዝቅተኛ ቁጠባ የሚታይባቸዉ ብሔራዊ መንግስታት አገራቸዉ ዉስጥ ከአቅማቸዉ በላይ የሆነ የገንዘብ እጥረት ሲያጋጥማቸዉ የሽያጭ ዋጋዉ በአገራቸዉ ገንዘብ ሳይሆን ያወጣናል ብለዉ በሚያምኑት በሌላ አገር ገንዘብ ለምሳሌ በዶላር ወይም በዩሮ የተተመነ ቦንድ እየሸጡ ገንዝብ የሚበደሩበት መንገድ ነዉ። የየአገሩ መንግስታት ቦንድ አየሸጡ ገንዘብ መበደራቸዉ አዲስ ክስተት አይደለም፤ ሆኖም መንግስታት በተለይ የታዳጊ አገሮች መንግስታት ቦንድ የሚሸጡት አገራቸዉ ዉስጥ በአገራቸዉ ገንዘብ ነዉ። ሉዓላዊ ቦንድን ልዩ የሚያደርገዉ ቦንዱ የሚሸጠዉ በአለም አቀፍ ደረጃ ሆኖ ሽያጩ የሚከናወነዉ ደግሞ በዉጭ ምንዛሪ መሆኑ ነዉ። ሉዓላዊ ቦንድ ሽያጭን ከመደበኛ ቦንድ ሽያጭ የሚለዩት ብዙ ነገሮች አሉ።
ሉዓላዊ ቦንድ ከሌሎች መደበኛ ቦንዶች ጋር ሲነፃፀር ብዙ ዉስብስብ ችግሮች አሉበት። ለምሳሌ ሉዓላዊ ቦንድ የሚገዙ አገሮች ወይም ድርጅቶች ቦንዱን የሚገዙት በዉጭ ምንዛሪ ነዉ፤ ሁለተኛ ሻጩ አገር ለቦንዱ የሚከፍለዉ ወለድ እጅግ በጣም ከፍተኛ ነዉ። በሦስተኛ ደረጃ ደግሞ ብዙዉን ግዜ ሉዓላዊ ቦንድ የሚሸጥ አገር ከቦንዱ ሽያጭ የሚያገኘዉ ገንዘብ ወለዱ የተቀነሰለት ገንዝብ ነዉ። ለምሳሌ በ10 በመቶ ወለድ የአንድ መቶ ሚሊዮን ዶላር ሉዓላዊ ቦንድ የሚሸጥ አገር እጁ ላይ የሚገባዉ ዘጠና ሚሊዮን ዶላር ሲሆን ብድሩን መልሶ ሲከፍል የሚከፍለዉ ደግሞ አንድ መቶ ሚሊዮን ዶላር ነዉ። ይህ ማለት ደግሞ ቦንድ ሻጩ አገር ወለዱን የሚከፍለዉ በተበደረዉ ገንዝብ ተጠቅሞበት ሳይሆን የተበደረዉ ገንዘብ ገና እጁ ላይ ሳይገባ ነዉ ወለዱን የሚከፍለዉ። ለሉዓላዊ ቦንድ የሚከፈለዉ ወለድ እጅግ በጣም ከፍተኛ ስለሆን ብዙ አገሮች በተለይ ታዳጊ አገሮች ሉዓላዊ ቦንድ መሸጥ የማይፈልጉት ይህንኑ ለብድሩ የሚከፈለዉን ከፍተኛ ወለድ ሰለሚፈሩ ነዉ።
የወያኔ አገዛዝ እንደተራ ወረቀት እየፈበረከ ገበያ ዉስጥ የሚበትነዉ ገንዘብና ከአገር ዉስጥ ባንኮች ከአቅሙ በላይ የሚበደረዉ ገንዝብ ኢትዮጵያ ዉስጥ የዋጋ ንረቱን ምን ያህል ሰማይ ላይ እንደሰቀለዉና የኢትዮጵያን ህዝብ ምን ያክል እንዳደኸየ ሁላችንም በግልጽ የምናዉቀዉ ሀቅ ነዉ። በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ የአገራችን ገበሬና ሠራተኛ የወያኔ ብልሹ የኤኮኖሚ ፖሊሲ ለአመታት ከፈጠረዉ የዋጋ ንረት በሽታ ሳይድን ነዉ ሌላ ሉዓላዊ ቦንድ የሚባል በቀላሉ የማይድን አደገኛ በሽታ ፊቱ ላይ የተደቀነበት።
ሉዓላዊ ቦንድ ደሃ አገሮች የሚሸጡትና ኃብታም አገሮች የሚሸጡት እየተባለ በሁለት ይከፈላል። ኃብታም አገሮች የሚሸጡትን ቦንድ ከነወለዱ ከፍለዉ ይጨርሳሉ ተብሎ በቦንድ ገዢ አገሮችና ድርጅቶችና ስለሚታመን እነዚህ አገሮች ለሚሸጡት ሉዓላዊ ቦንድ የሚከፍሉት ወለድ ዝቅተኛ ነዉ። ኢትዮጵያን መሰል ደሃ አገሮች ግን ብድር የመክፈል ችሎታቸዉ አስተማማኝ ስላልሆነ ሉዓላዊ ቦንድ ሲሸጡ ለቦንድ ገዢዉ የሚከፍሉት ወለድ እጅግ በጣም ከፍተኛ ነዉ። ስለሆነም ደሃ አገሮች በተለይም እንደ ኢትዮጵያ አይነቶቹ ለመጀመሪያ ግዜ ሉዓላዊ ቦንድ ለሚሸጡ አገሮች ቦንድ ለመሸጥ ከመወሰናቸዉ በፊት ማስተካከል ያለባቸዉ ብዙ ነገሮች አሉ። በነገራችን ላይ ሉዓላዊ ቦንድ መሸጥ በራሱ ምንም ጥፋት የለበትም። እንዲያዉም ህዝባዊና አገራዊ ሃላፊነት የሚሰማቸዉ መንግስታት ሉዓላዊ ቦንድ በመሸጥ የፋይናንስ ጉድለታቸዉን በመሸፈን የአገራቸዉን እድገት አቅጣጫ ቀይሰዉ ጠንካራ ኤኮኖሚ የመገንባት አቅም ማግኘት ይችላሉ። በኛም አገር ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎቸ አንደኛ አገራዊ ሃላፊነት ቢሰማቸዉ፤ ሁለተኛ በአቅማቸዉ ቢኖሩ፤ ሦስተኛ በአገር ስም የተበደሩትን ገንዘብ መዝረፍ አቁመዉ ሁሉንም ለአገር ጥቅም ቢያዉሉትና ተበድረዉ በሚሰሯቸዉ ፕሮጀክቶች ሁሉም ኢትዮጵያዊ እኩል ተጠቃሚ ቢሆን አገራችን መደበኛ ቦንድም ሆነ ሉዓላዊ ቦንድ በመሸጥ የምትበደረዉ ገንዘብ ብሄራዊ አቅም ስለሚገነባ ዕዳዉ ብዙም አያስፈራንም። ችግሩ ያለዉ ሉዓላዊ ቦንድ መሸጡ ላይ ሳይሆን እዚህ ዉሳኔ ላይ ከመደረሱ በፊት መወሰድ ያለባቸዉን እርምጃዎች በጥንቃቄ መዉሰዱ ላይ ነዉ። የወያኔም ትልቁ ችግር ያለዉ እዚህ ላይ ነዉ። የቦንዱ ሽያጭ ይዞት የሚመጣዉን ጣጣና ፈንጣጣ ግምት ዉስጥ ሳያስገባ ነዉ ሉዓላዊ ቦንድ እሸጣለሁ ብሎ ያወጀዉ።
የወያኔ አገዛዝ የበጀት ዲሲፕሊን የሌለዉ፤ በአቅሙ የማይኖር፤ እመራዋለሁ የሚለዉን አገር ኃብት የሚዘርፍና በሚያደርጋቸዉ ነገሮች ሁሉ ኢትዮጵያን የማያስቀድም የአገርና የህዘብ ጠንቅ የሆነ ክፉ አገዛዝ ነዉ።ኢትዮጵያን ጨምሮ በመላዉ አለም የሚኖሩ ኢትዮጵያዉያን የወያኔ ፓርላማ የሉዓላዊ ቦንድ ሽያጭ ረቂቅ ህግ አፀደቀ ሲባል ቀልባቸዉ የረገፈዉ ከላይ የተጠቀሱትን የወያኔ ጠባዮች በሚገባ ሰለሚያዉቁ ነዉ። ወያኔ ከአገር ዉስጥም ሆነ ከአገር ዉጭ የብድር ምንጮች በሚበደረዉ ገንዘብ መንገድ፤ ህንፃና ግድብ ሊሰራ ይችላል። እነዚህ ነገሮች በመሰራታቸዉ የሚከፋ ኢትዮጵያዊ ያለ አይመስለንም። ብዙ ኢትዮጵያዉያንን የሚከፋቸዉ ወያኔ በነሱ ስም በተበደረዉ ብድር በጀመራቸዉ ፕሮጀክቶች ሁሉ መጠቀም አለመቻላቸዉና በገዛ አገራቸዉ የበይ ተመልካች መሆናቸዉ ነዉ። እዚህ ላይ የህዳሴዉን ግድብ አንደ ምሳሌ ወስደን መመልከት እንችላለን። የህዳሴዉን ግድብ የእንጂኔሪንግ ኮንትራት ያለምንም ጨረታ አሸንፎ ከፍተኛ ትርፍ የሚያጋብሰዉ መስፍን ኢንጂኔሪንግ የተባለ የወያኔ ድርጅት ነዉ። ለህዳሴዉ ግድብ ማሰሪያ ሲሚንቶ የሚያቀርበዉ የወያኔዉ መሶብ ሲሚንቶ ፋብሪካ ነዉ። ለግድቡ ፕሮጀክት የትራንስፖርትና ማጓጓዣ አገልግሎት የሚሰጡት የአዜብ መስፍን ዘመዶች ናቸዉ;፡ ለህዳሴዉ ግድብ ሰራተኞች የምግብ አገልግሎት የሚሰጡት የወያኔ ኩባንያዎች ናቸዉ። የህዳሴዉን ግድብ እንደምሳሌ ወሰድነዉ እንጂ ኢትዮጵያ ዉስጥ በብድርም ሆነ በእርዳታ ገንዘብ በሚሰሩ ፕሮጀክቶች ሁሉ ተጠቃሚዉ ወያኔና ባለ ሟሎቹ ናቸዉ። ወያኔ እንደ ተራራ የቆለለዉን ብድር እስከነወለዱ የሚከፍለዉ ግን የኢትዮጵያ ህዝብ ነዉ።
የአለም ባንክንና አለም አቀፉን የገንዝብ ድርጅት ጨምሮ ብዙ የኤኮኖሚ ሳይንስ ጠበብቶች አገሮች በተለይ የዉጭ ዕርዳታ ጥገኛ የሆኑ ደሃ አገሮች ሉዓላዊ ቦንድን አገር ዉስጥ ለሚያጋጥማቸዉ የገንዘብ ጉድለት ማሟያ አድረገዉ እንዳይጠቀሙ በተከታታይ ያስጠነቅቃሉ። የወያኔ አገዛዝም ይህ ማስጠንቀቂያ በተከታታይ ከደረሳቸዉ መንግስታት አንዱ ነዉ። ሆኖም የማንንም ምክር የማይሰማዉ ወያኔ ጆሮ ዳባ ልበስ ብሎ ሉዓላዊ ቦንድ በመሸጥ መዘዙ ከትዉልድ ወደ ትዉልድ የሚተላለፍ ክፉ በሽታ እየዘራ ይገኛል። ወያኔ እስከዛሬ የተበደረዉ ብድር ምኑም ሳይከፈል ሉዓላዊ ቦንድ ከጀመረ በእናት አገራችን ላይ እንደ ትልቅ ተራራ የሚቆለለዉን ብሄራዊ ዕዳ የምንከፍለዉ እኛ የዚህ ዘመን ኢትዮጵያዉያን ብቻ ሳንሆን ገና ያልተወለዱ የልጅ ልጆቻችን ጭምር ናቸዉ።
ኢትዮጵያ ኤኮኖሚዋ ያልዳበረ ደሃ አገር በመሆኗ አበዳሪ አገሮችን ብድር ሰርዙልኝ ብላ ሳትወተዉት፤ የብድር ክፊያ ግዜዋን ሳታራዝም፤ ወይም የብድር ዉል ማሻሻያ ጥያቄ ሳታቀርብ እስከዛሬ የተበደረችዉንና ለወደፊትም የምትበደረዉን የዉጭና የአገር ዉስጥ ብድር የመክፈል ሃላፊነቷን ጤናማ በሆነ መልኩ መወጣት የምትል አገር አይደለችም። እንደዚህ የምንለዉ ደግሞ ወያኔንና ዘረኛ ስርዐቱን ስለምንጠላ ሳይሆን በሚከተሉት ማስረጃዎች ላይ ተንተርስሰን ነዉ። 1ኛ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ዕዳና አጠቃላይ አገራዊ ምርት (GDP) መጧኔ ቁጥሩ ከፍተኛ ነዉ።
ይህ ማለት ኢትዮጵያ የተቆለለባት ዕዳና ቤሄራዊ ገቢዋ ይቀራረባሉ፤ እኩል ናቸዉ ወይም ዕዳዋ ከገቢዋ ይበልጣል ማለት ነዉ። 2ኛ የአገራችን የዉጭ ብድርና የዉጭ ንግድ ገቢ መጣኔ እጅግ በጣም ከፍተኛ ነዉ። ይህ ማለት ደግሞ ምርታችንን ለአለም ገበያ አቅርበን የምናገኘዉ የዉጭ ምንዛሪ ከዉጭ አገር ዕቃ ሊገዛልን ቀርቶ የተበደርነዉን ብድር ወለዱንም መክፈል አይችልም ማለት ነዉ። 3ኛ የወያኔ አገዛዝ የብድር ዕዳና አገዛዙ አገር ዉስጥ በግብር መልክ የሚሰበስበዉ ገቢ መጣኔ እጅግ በጣም ከፍተኛ ነዉ። ቀለል ባለ አማርኛ የወያኔ አገዛዝ ሁሉንም ነገር ትቶ በሚሰበስበዉ ገንዘብ ዕዳዉን ብቻ ቢከፍል ከእዳዉ ለመላቀቅ ብዙ አመታት ይፈጅበታል።
ለእናት አገራቸዉ ለኢትዮጵያ የሚጨነቁ ኢትዮጵጵያዉያን የወያኔ ፓርላማ በቅርቡ ያፀደቀዉን የሉዐላዊ ቦንድ ሽያጭ ህግ አጥብቀዉ የሚቃወሙት እነዚህን ሁሉ ገሃድ የወጡ የአገራችንን ችግሮች በሚገባ ስለሚያዉቁ ነዉ። ለኢትዮጵያና ለህዝቧ እንጨነቃለን ስንል ደግሞ እንደ ወያኔ “እኔ ከሞትኩ ሠርዶ አይብቀል” በሚል የንፉጎች አባባል ተዉጠን አይደለም። ለትናንትናዋ ኢትዮጵያ እንደተጨነቅን ሁሉ ለዛሬዋ፤ ለነገዋና እኛ ካለፍን በኋላ ለሚመጣዉ ኢትዮጵያዊ ትዉልድም እኩል እንጨነቃለን። ለዚህም ነዉ የሉዓላዊ ቦንድ ሽያጩን ብቻ ሳይሆን ወያኔ ያመጣብንን መዐት ሁሉ ለማስቆምና አገራችንን በትክከለኛ የእድገትና የዲሞክራሲ መሠረቶች ላይ ለማስቀመጥ ወያኔ መወገድ አለበት ብለን የሞት የሽረት ትግል የጀመርነዉ።

በሰላማዊ ተቃዋሚዎች ላይ የደረሰውን ጥቃት እናወግዛለን !!!


በአብዛኛው በወጣት ወንዶችና ሴቶች የተገነባው ሰማያዊ ፓርቲ አባል የሆነበት የዘጠኝ ፓርቲዎች ኅበረት፣ “ነፃነት ለፍትሃዊ ምርጫ” የተሰኘ የአንድ ወር መርሀ ግብር አውጥቶ፤ ችግሮችን ተጋፍጦ አብዛኛውን ተግባራዊ አድርጓል። የመርሀ ግብሩ አቢይ አካል የነበረውና በህዳር 27 እና 28 ሊከናወን ታድቆ የነበረው የ24 ሰዓት የአደባባይ ተቃውሞ ግን በአገዛዙ የኃይል እርምጃ ምክንያት በታቀደው መንገድ ሊከናውን አልቻለም። የህወሓት ቅልብ የሆኑት ሲቪል የለበሱ ሰላዮችና የፌደራል ፓሊስ በተቃውሞው ተሳታፊዎች ላይ ኢሰብዓዊ የሆነ ጥቃት ፈጽመዋል።
ከጅምሩ፣ የፓርቲዎቹ ኅበረት የተቃውሞ ማሳወቂያ ደብዳቤውን ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለማስገባት የገጠመው ችግር የህወሓት አገዛዝ የመንግሥትን መዋቅር ለፓርቲ ሥራ፤ የመንግሥት ተቀጣሪዎችን ደግሞ እንደ ህወሓት አገልጋዮች የሚጠቀምባቸው መሆኑ አንዱ ማሳያ ሆኗል። ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚያደርጉ ማሳወቅ የፈለጉት ፓርቲዎች ህወሓት የዘረጋውን አፋኝ ሥርዓት የሚታገሉ በመሆናቸው ብቻ ደብዳቤዓቸውን የሚቀበል እንኳን አጥተው ተጉላልተዋል። ለሰልፉ ቅስቀሳ ማድረግም በራሱ እንደ ወንጀል ተቆጥሮ ወጣቶች ተንገላተዋል፣ ተደብድበዋል፣ ታስረዋል። ያም ሆኖ ውጣ ውረዶች ታልፈው ቅዳሜ ህዳር 27 ቀን 2007 ዓ. ም. ደረሰ።
የኅበረቱ አመራሮች፣ አባላት፣ ደጋፊዎችና ጥሪውን የሰማ ሕዝብ ወደ መስቀል አደባባይ ማምራት ሲጀምር ሲቪል የለበሱ የአገዛዙ ታጣቂዎች እና ፌደራል ፓሊሶች ከሰንደቅ ዓላማዎችና መፈክሮች ባለፈ አንዳች ነገር ያልያዙትን እድሜያቸው ከሃያዎች ያልዘለሉ ውድ የኢትዮጵያ ልጆችን ደብድበዋል፤ ብዙዎቹም አፍነው በአሰቃቂ ሁኔታ እያንገላቱ ወደ እስር ቤቶች ወስደዋል። ወጣቶች ተወልደው ባደጉበት አገር፤ ስሜታቸውን በነፃነት ለመግለጽ በመድፈራቸው ብቻ በጭካኔ ተረግጠዋል፤ ተፈንክተዋል፤ እጅና እግሮቻቸው ተሰብሯል።
ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ይህ የህወሓትን ፋሺስታዊ እርምጃ አጥብቆ ይቃወማል። ግንቦት 7፣ ህወሓት ከስልጣን እስካልተወገደ ድረስ እንዲህ ዓይነቱን ፋሺስታዊ ተግባር መፈፀሙን የማይተው እኩይ ኃይል እንደሆነ ያውቃል፤ በዚህም ምክንያት የትግላችን ግብ ህወሓትን ማስወገድና በምትኩ የኢትዮጵያ ሕዝብ ይሁንታ ያገኘ መንግሥት መመሥረት መሆን ይኖርበታል ብሎ ያምናል፤ ለዚህም ይታገላል።
ግንቦት 7፣ ህዳር 27 ቀን 2007 ዓ.ም. “መብቶቻችንን በህወሓት ዘረኛ አምባገነኖች አናስነጥቅም” በማለት አደባባይ የወጡ ወጣቶችን ጽናት ያደንቃል። ህወሓት የሚለውን ሳይሆን የይስሙላ ህጉ የፈቀደላቸውን ለማድረግ በመድፈራቸው በህወሓት የህግ ማዕቀፍ ውስጥ ሆኖ የሚደረገውን ትግል አንድ እርምጃ ወደፊት አራምደውታል።
እያንዳንዱ የፓለቲካ ድርጅት ከዚህ ኩነት የሚወስዳቸው ተጨማሪ ትምህርቶች ቢኖሩም የሚከተሉትን ነጥቦች ብዙዎችን ያስማማሉ ብለን እናምናለን።
1. ህወሓት በምንም ዓይነት ቢሆን የያዘውን ስልጣን ለሕዝብ ፈቃድ ማስገዛት አይፈልግም፤
2. ህወሓት አገራችን ወደ ትርምስ እየገፋት እንደሆነ ግልጽ እየሆነ መጥቷል፤
3. ስልጣኑን የሚያሳጣው ከመሰለው እና አቅሙ እስካለው ድረስ ዘግናኝ እርምጃዎችን ከመውሰድ አይመለስም፤
ከህወሓት አገዛዝ መገላገል የሚቻለው ተገዶ ሲወገድ ብቻ ነው። ህወሓት እንዲወገድ ደግሞ የመጨቆኛ አቅሙ መዳከም ይኖርበታል። ህወሓትን የማስወገጃ አማራጭ መንገዶች ብዙ ሲሆኑ ተቀናጅተው ቢሠሩ የበለጠ ውጤታማ ይሆናሉ ብለን እናምናለን፤ “ሁለገብ ትግል” የምንለው የትግል ስልት ጭብጥ ይህ ነው። “እምቢ ለነፃነቴ” ብሎ የተነሳ ሕዝብ ህወሓትን ምን ያህል እንደሚያስደነግጥ በተደጋጋሚ ታይቷል። ህዳር 27ን መንደርደሪያ አድርገን በመውሰድ ከዚህ በተሻለ ለተደራጀ ሕዝባዊ እምቢተኝነትና አመጽ ራሳችን እናዘጋጅ።
በዚህ አጋጣሚ ግንቦት 7፣ ለመከላከያ ሠራዊት እና ፓሊስ አባላት ተደጋጋሚ ጥሪዎችን ማድረግ ይሻል። የመከላከያ ሠራዊት እና ፓሊስ አባላት እንደማንኛውም የኢትዮጵያ ዜጋ በህወሓት ዘረኛና አምባገነን አገዛዝ የተበደላችሁ መሆኑን እናውቃለን። የህወሓት ሹማምንት ከሆኑ አዛዦቻችሁ መላቀቅና ራሳችሁን ነፃ የማውጣት ኃላፊነት የወደቀው በእናንተው በራሳችሁ ላይ ነው። ሠራዊቱ ራሱን በራሱ ነፃ ማውጣት ይኖርበታል። የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር ህወሓት መወገዱ የማይቀር በመሆኑ ሠራዊቱ ራሱን ነፃ አውጥቶ ከሕዝብ ጋር ካልወገደ እጣ ፈንታው የተሸነፈ ሠራዊት መሆን ነው። ከዚህ በላይ የሠራዊቱ አባል እየደበደበ ያለው የራሱን ልጅ፣ ወንድሙን ወይም እህቱን እንደሆነ ይወቅ። ይህ ወሳኝ ጊዜ ነው እያንዳንዱ የሠራዊቱ አባል በግል ኃላፊነት ያለበት መሆኑ ሊሰማው ይገባል።
በሁሉም ዓይነት የትግል ዘርፎች የኢትዮጵያ ወጣቶች በስፋት እየተቀላቀሉ መሆኑ ተስፋ ሰጪ ነው። ጊዜው የለውጥ ነው። የተለያዩ ስትራቴጂዎች ተደጋግፈው እንዲሄዱ መደረግ ያለበት ወቅት ላይ ነን። በህዳር 27 ቀን በህወሓት ቅልብ ሰላዮችና የፌደራል ፓሊሶች አማካይነት የደረሰው ጉዳትና የፈሰሰው ደም ለፍትህና ለነፃነት የተከፈለ ዋጋ ነው። ህመማችሁ ህመማችን፤ ትግላችሁ ትግላችን ነው። የተለያዩ መንገዶች ወደ ነፃነት አደባባይ እያመሩ ነው።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!

የህወሃት ምርጫ የህዝብ መከራ!

 


ህወሃቶች እኛ ከሌለን ይህችን አገር እንበትናታለን፤ ይህችን አገር የምንሰብር እኛ የምንጠግን እኛ እያሉ እንደሚያሟርቱ ሰምተናል። እኛ የቀረፅነው ፖሊስ ከሚቀየር ሞታችንን እንመርጣለን እያሉ ማቅራራታቸውም ከህዝብ የተሰወረ ነገር አይደለም። የህወሃት ፖሊሲ የሚቀየረው በመቃብርችን ላይ ነው የሚል የማይናወፅ አቋማቸው መቼም ቢሆን በሠለጠነ መንገድ በውይይትና በድርድር እንደማይቀየር ደጋግመው አሳይተውናል። ህወሃቶችን በሠለጠነ መንገድ ተደራድሮ እና ሰጥቶ በመቀበል መርህ ለለውጥ አዘጋጃለሁ ማለት ከእባብ የእርግብ እንቁላል እንደመመኘት ያህል ነው። ከእባብ የእርግብን ዘር የሚጠብቅ ማን ነው?
እንግዲህ ህወሃቶች ይህን የመሰለ የከረረ አቋም ይዘው ምርጫ ለምን ያደርጋሉ ብሎ መጠየቅ ተገቢ ይሆናል። ይሄ ህወሃቶች ለኢትዮጵያና ለህዝቧ ራዕይ የሌላቸው ከመሆን የሚመነጭ ነው። ድርጅቱ ራዕይ አልባ የሆነው ደግሞ በህወሃት ውስጥ የተሰባሰቡ ግለሰቦች ራዕይ አልባ በመሆናቸው ነው። ህወሃቶች የሚኖሩለትም ሆነ የሚሞቱለት ቁም ነገር ከመብልና መጠጥ የዘለለ አይደለም። ህወሃቶች ራዕይ ቢኖራቸው ኑሮ በታሪክ የሚያስወቅሳቸውንና የህዝቡን ፍቅር የሚያሳጣቸውን እኩይ ተግባራት ባልፈፀሙ ነበር። ራዕይ የሌላቸው በመሆኑ ለሚፈፅሙት ወንጀል ሁሉ ገደብ እንዳይኖራቸው ሆኑ። ራዕይ ያለው ሰውም ሆነ ድርጅት እኔ ብቻ አይልም። ራዕይ የሰነቀ ድርጅትም ሆነ ሰው ከራሱ ክበብ አልፎ ሌላው እንደምን ሁኖ በሠላም እና በደስታ እንደሚኖር ያስባል እንጂ ዕለት ዕለት ደም በማፍሰስ አይኖርም።
ህወሃት በምርጫ ስልጣኑን እንደማይለቅ ለራሱ የማለ ድርጅት ነው። እዚህ መሃላ ላይ ያደረሰው ደግሞ እስከ ዛሬ የፈፀማቸው ወንጀሎቹ ናቸው።የጨበጠውን ስልጣን በምርጫ ቢለቅ ነገ የሚከተለውን ጠንቅቆ ያውቃል። ትላንት ያፈሰሱት የንፁሃን ደም ከኢትዮጵያ ምድር ላይ እየጮኸ ነው። ዘርፈው የገነቡት ህንፃ በአዲስ አበባ ጎዳናዎች ላይ ቆመው ሌብነታቸውን እየመሰከሩባቸው ነው። በልማት ሥም ከኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ተዘርፎ የተደራጀው የንግድ ተቋም በኢትዮጵያ ህዝብ ወዝና ደም ታጥኖ እንዳማረበት አለ። ህወሃት የኢትዮጵያ የህዝብ ጠላት ሆኖ ራሱን ያቆመ ቡድን በመሆኑ በሰላማዊ እና በሰለጠን መንገድ የያዘውን ሥልጣን ለህዝብ አይለቅም።
እንግዲህ ምን ይሻላል ?
ህወሃቶች ኑና እንወዳደር ብለዋል። እነዚህ ቡድኖች ኑና እንወዳደር ሲሉ እነርሱ የብረት ቦክስ ጨብጠው፤ ሌሎቹ ደግሞ ሌጣቸውን ሁነው ያለ በቂ ታዛቢ እንዲፎካከሯቸው ወስነው ነው። እንዲህ ባለ ሁኔታ ውስጥ ሁነንም ቢሆን የምንወዳደረው ለነፃነት መሆን ይኖርበታል። ከነፃነት በመለስ ያለው ማንኛውም ዓይነት የምርጫ ውጤት በአገራችን እየተካሄደ ያለውን ዝሪፊያ፤ ዘረኝነት፤ እሥራት እና ግድያ ያስቆማል የሚል ዕምነት በማንም ዘንድ ያለ አይመስለንም። በምርጫ ውድድር የምናተርፈው የህግ የበላይነት፤ እኩልነት እና ነፃነት ካልሆነ ተጎጂው ሰፊው ህዝብ ይሆናል።
ህወሃት የብረት ቦክስ ጨብጦ እኛ ደግሞ ሌጣችንን ሁነን መወዳደር ፍትሃዊ አይደለም በማለት ድምፃቸውን እያሰሙ ያሉት ወገኖችም የህዝብን መሠረታዊ ፍላጎት ለሟሟላት አስፈላጊ የሆነው ነፃነት ዋነኛው ግባቸው መሆን ስለሚኖርበት ይመስለናል። ወደ ውድድር ከመግባታችን በፊት ህወሃት የብረት ቦክሱን ያውልቅ፤ የመወዳደሪያ መድረኩም እኩል ይሁን ማለታቸው የሚሰማ ቢኖር ፍትሃዊ ጥያቄ ነው።የህወሃትን የብረት ቦክስ ለማስወለቅ መሥዋዕትነት ለመክፈል መዘጋጀታቸውም ለነፃነት የሚከፈል ዋጋ ይሆናል። ከህወሃት ጭካኔና ድንቁርና ስንነሳ በዚህ መንገድ የሚሄዱት የሚከፍሉት መሥዋዕትነት ከባድ እንደሚሆን እንጠብቃለን። ግን ደግሞ ነፃነት ያለ መሥዋዕትነት እንደማይገኝ ሌላው ቀርቶ ነፃነትን የማያውቁት ህወሃቶች ያውቃሉ። በማንኛውም መልኩ ከህወሃቶች ጋር አገት ለአንገት ተናንቀው በአገር ቤት ውስጥ እየተንቀሳቀሱ ያሉት ድርጅቶች ልበ ሙሉነታቸውን እጅግ አድርገን እናደንቃለን። እምቢ ለነፃነቴ፤ እምቢ ለክብሬ፤ እምቢ ለህወሃቶች ቀይ መስመር ማለት ይሄ እንጂ ሌላ አይደለም። እንግዲህ ዘረኞቹና ዘራፊዎቹ ቡድኖች ሊያደርሱ የሚችሉትን ጉዳት መቀነስ የሚቻልበትን መንገድ ማሰብ ተገቢ ይሆናል። ህዝቡ በልዩ ልዩ ሰንሰለት የታሠረ በመሆኑም በሚፈለገው መጠን ወጥቶ የትግሉ አካል ካልሆነም ተስፋ መቁረጥ አይገባም።በተጀመረው ላይ ይበልጥ እያጠናከሩና እየጨመሩ እየተካሄደ ያለውን ትግል መቀጠል ምርጫ የሌለው ሥራ ነው።
ግንቦት ሰባት የፍትህ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ አገር ቤት ሁነው ከጭካኔ በቀር ሌላ ዕውቀት ከሌላቸው ህወሃቶች ጋር በትግል ላይ ያሉ ድርጅቶችን ያደንቃል። ያመስግንማል። በርቱ ከማለት በቀር የምንለው ሌላ የለንም።
እኛ የጀመርነውን ሁለ ግብ ትግል እያጠናከርነው ነው። የአገራችንን ውርደት፤ የወገኖቻችንን ጉስቁልና እያየን ዝም ብንል እርግማን ይሁንብን ያሉ ወጣቶች የአያቶቻቸውን ጋሻና ጦር አንስተዋል። እናቶችም ልጆቻቸውን መርቀው ፋኖ ተሠማራ ብለዋል። ሌሎች ደግሞ የኋላ ደጀን ሁነው ሳያቅማሙ ቁመዋል። ብዙ ባለሙያዎች ለአገራቸው የሚከፈልውን መሥዋዕትነት ለመክፈል ተዘጋጀተዋል።
እንግዲህ የጀመርነውን ትግል የሚያስቆመን ምድራዊ ኃይል የለም። የህወሃት የመረጃ መረብ ይበጣጠሳል። የጦር ኃይሉ ከጥቂት ዘረኞችና ሌቦች ይልቅ ወገኑን እንደሚመርጥ በየቀኑ የሚደርሱን መረጃዎች ያሳዩናል። የከተማው ህዝብ ህወሃቶችን አክ እንትፍ ካላቸው ብዙ ዘመን ሁኖታል። የገጠሩም ህዝብ የህወሃት ዋሻ የመሆኑ ነገር አብቅቷል። ይሄ ሁሉ የእኛ አቅማችን ነው። ይሄን አቅም አደራጅተንና ሥራ አሲይዘን አገራችንን ነፃ የምናወጣበት ግዜ ሩቅ አይደለም።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !

Thursday 4 December 2014

ፍርደ ገምድሉ የወያኔ ፍርድ ቤት ከግንቦት 7 ጋር በተያያዘ ለተከሰሱት የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጠ


አሸባሪው የወያኔ አገዛዝ ትንታግ የሆኑትን ወጣት ፖለቲከኞች በሽብር ወንጀል ተካፍለዋል፣ ድርጊቱን ለመፈጸም ተንቀሳቅሰዋል፣ ህዝብን ለአመጽ ቀስቅሰዋል በሚል የፈጠራ ክስ አጎሮ ስቃይ እየፈጸመባቸው ሲሆን የካንጋሮው ፍርድ ቤት አራቱ ወጣት ፓለቲከኞችን እና በተመሳሳይ መዝገብ የተከሰሱት ሌሎች 6 ተከሳሾች ለቀረበባቸው የፈጠራ ክስ መቃወሚያ እንዲያቀርቡ ለታህሳስ 9 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱ ታውቋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ አለማቀፍ የሰብአዊ መብት ድርጅቶች አገዛዙ በወጣት ፖለቲከኞች ላይ ያቀረበውን የፈጠራ ክስ እያወገዙ መቀጠላቸው ታውቋል። ወጣት ፖለቲከኞቹን ጨምሮ በአገዛዙ የፈጠራ ክስ ሰለባ ሆነው በእስር እየተሰቃዩ የሚገኙትን የህሊና እስረኞች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ አገዛዙ በአስቸኳይ እንዲፈቱ የሚጠይቅ የበይነ መረብ ዘመቻ መከፈቱም የታወቀ ሲሆን በርካታ ኢትዮጵያውያን ዘመቻውን በመደገፍ ፋሽስታዊው አገዛዝ ሁሉንም የህሊና እስረኞች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በአስቸኳይ እንዲፈታ አበክረው እየጠየቁ እንደሚገኙ ዘጋቢያች አመልክቷል።
በሌላ ዜና የፋሽስቱ ወያኔ አገዛዝ እያደረሰባቸው ያለው ወከባ፤ አፈናና እስር ትግሉ እንደማይቆም የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር አስታወቀ። “ነጻነታችን በእጃችን” ነው የሚለው ትብብሩ፣ ፋሺስታዊው አገዛዝ እየወሰዳቸው ባሉት እርምጃዎች ፈጽሞ ወደኋላ እንደማይል በማሳሰብ እቅዱን በህጋዊ መንገድ ለማስቀጠል እስከ ህይወት መስዋትነት ለመክፈል ያለውን ቁርጠኝነት ገልጿል።
በመጨረሻም አገዛዙ ከአፈና ድርጊቱ እንዲገታና ለቀረበው ህጋዊ የዕውቅና ጥያቄ በአስቸኳይ መልስ እንዲሰጥ የጠየቀው የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር የትግሉ አላማ የመድብለ ፓርቲ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ መሆኑን በማመልከት በአገር ውስጥም ሆነ ከአገር ውጪ የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ለቀጣዩ ትግል የሚቀርበውን ጥሪ በንቃት እንዲከታተሉና ከፓርቲዎች ጎን እንዲቆሙ፣ ትብብሩን ያልተቀላቀሉ ፓርቲዎችም እንዲቀላቀሉ ጥሪ አቅርቧል።

ለሀገር ነጻነት የወጣቱ ተሳትፎ ቀጣይነት ይኑረው!


ከ1997 ምርጫ ማግስት ጀምሮ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ወጣቶችና በሁሉም የእድሜ ክልል የሚገኙ ዜጎች ለሀገራቸው የዲሞክራሲ መብት መከበር እያደረጉት ያለው አስተዋጽኦ ላቅ እያለ መምጣቱ የቅርብ ጊዜ ትውስታ ነው። ይህን ተከትሎ ዛሬ ወጣቱ የወላጆቻችን ደምጽ ይከበር፣ ኢትዮጵያዊነት በዘረኝነት አይፈተንም! ነጻነት ዳቦ አይደለም! እስራትና ግድያ በኢትዮጵያ ይቁም! የወያኔ አገዛዝ በቃን! በሚሉ በበርካታ ወጣቶች ጩኸት የወያኔ ሹማምንትና አገልጋዮቹ ላይ የፈጠረው ድንጋጤ ወጣቱን ሽብርተኛ አስደርጎታል።
ወጣቶች ህዝብን አስተባብረው ለተቃውሞ በማሳደም የወያኔን ዘረኝነት በመቃወም ረገድ የተለያዩ ዘዴዎችን ከሌሎች የነጻነት አቢዎት እንቅስቃሴ በመማር እምቢተኝነትን በማሳየት ጅማሮ ላይ ናቸው። ሰሞኑን በባህርዳር ከተማ የተጀመረው የእምቢተኝነት ዘመቻ በሚቀጥለው በሁሉም የሀገሪቱ ክፍል ይቀጣጠል ዘንድ ወጣቱ ሃላፊነት አለበት። ሀገራችን መስቀለኛ መንገድ ላይ ነች። ሁሉም የማህበረሰብ ክፍል ወያኔን ለማስወገድ በሚደረገው መራራ ትግል ውስጥ የበኩሉን አስተዋጽኦ ማድረግ ይኖርበታል። አባቶቻችን የውጪ ሀገራትን ወራሪዎች ወራራ ለመመከት ሁሉም ሰው የሚችለውን ሁሉ እንዲያደርግ ያደረጉት ጥሪ አሁንም ላይ ይሰራል።
ለራሳችን ክብር፣ አንድነት፣ ለሀገር ነጻነትና ህልውና መከበር ኢትዮጵያዊ እምቢተኝነት የሚጀምረው ከትንሽ ነው። ህወሃት በጠላትነት የፈረጃችሁ የዛሬ ወጣቶች የሆናችሁ ዘመን በሚፈቅድላችሁ ቴክኖሎጂ በመጠቀም በመላው ሀገሪቱ ወረቀት ከመበትን አንስቶ ሌሎች ይትግል ስልቶችን ተጠቀሙ። ኢትዮጵያ ሀገራችሁ በአንድ ጠባብ ዘረኛ ቡድን መዳፍ ውስጥ ማልቀስ ከጀመረች ሰነባብታለች። ዜጎቿ የግለሰብም ሆነ የቡድን መብታቸው ተረግጦ በባርነት እየተገዙ ነው። ጉልበታቸውና ሀብታቸው እየተመዘበረ ሲሆን፤ ለነጻነት፣ ለዲምክራሲና ለፍትህ የጮኹ ሁሉ ሽብርተኛ ተብለው ወደ ማጎሪያ እየተወረወሩ ነው።
ስለዚህ ስለ ሀገራችን፣ ስለራሳችን የግልም ሆነ የቡድን ጥቅም ስንል በሀገሪቱ የትኛውም ከፍል የተጀመረውን የእምቢ አልገዛም ባይነት እንቅስቃሴ እንደግፍ፣ እንሳተፍ! በባህርዳር የተጀመረውን የወጣቶች እንቅስቃሴን አድንቀን ይህ ተነሳሽነት በሌላውም የሀገሪቱ ክፍል መቀጠል ያለበት ነው።
ይህን በማድረግ ወደ ትግሉ በመቀላቀል ካልተሳተፍን በስተቀር ትግላችን አንድ እርምጃ ወደፊት ፈቀቅ ማድረግ እንደማንችል ግንቦት 7 ያምናል። ስለሆነም ሁሉም አካላት በያለበት በየሚኖርበት፣ በሚችለው አቅሙ ሁሉ ወደትግሉ በንቃት ተሳተፍ! አብረን ታግለን ነጻነታችንን እናረጋግጥ! ለኢትዮጵያ ትንሳኤ፣ የነጻነት አዋጆች ነጋሪ፣ አብሳሪ ትውልዶች እንሆን ዘንድ ሳንታክት እንታገል ዘንድ ወቅቱ የሚጠይቀው ጥሪ ነው።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ

Thursday 27 November 2014

ተማሪዎች፣ መምህራን እና የተቋማት ፕሬዚዳንቶች ለአመጽ ተነሱ!


ዘረኛውና አምባገነኑ የህወሓት አገዛዝ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ከካድሬ ማሰልጠኛ ማዕከላትነት ለይቶ የማያይ ስለመሆኑ በተቋማቱ ውስጥ የሚደረጉ ተግባራት ማረጋገጫዎች ናቸው። ለዚህ ተግባሩ በሰነድ ደረጃ መቅረብ ከሚችሉት የቅርብ ጊዜ ማስረጃዎች ዋነኛው በህዳር 2007 ዓ.ም. በሥራ ላይ የዋለው “የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የኢህአዴግ የምርጫ ድል ልማት ሰራዊት ግንባታ አደረጃጀት ማንዋል” የተሰኘው በትምህርት ሚኒስቴር ተዘጋጅቶ ለሁሉም ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የተላለፈው ሰነድ ነው። ይህ ሰነድ፣ የህወሓት አሳፋሪ የትምህርት ፓሊሲ ባፈጠጠ መልኩ የተገለፀበት፤ የኢፌዴሪ መንግሥት ተብሎ በሚጠራው የህወሓት አገዛዝ ተቋም እና በህወሓት/ኢህአዴግ ፓርቲ መካከል ለይምሰል እንኳን ልዩነት አለመኖሩ በግላጭ የሚታይበት ሰነድ በመሆኑ በዚህ ርዕሰ አንቀሳችን በስፋት ልንዳስሰው ወስነናል።
ሰነዱ በትምህርት ሥርዓቱ ላይ መርዙን መርጨት የሚጀምረው ገና በመግቢያው ስለማንዋሉ አስፈላጊነት ሲገልጽ ነው። ማንዋሉ “ከምንም በላይየብጥብጥና የሁከት መንስኤ የሆነውን ተማሪ በኢህአዴግ አመራር አባላት እየታገዙ ለመያዝ የሚያስችል ነው” በማለት ህወሓት ተማሪውን የሚመለከተው “ከምንም በላይ በብጥብጥ መንስኤነት” መሆኑ፤ ለዚህ መድሀኒቱ ደግሞ ተማሪውን በኢህአዴግ አመራር አባላት “መያዝ” መሆኑን በማያሻማ ሁኔታ ይገልፃል። ቀጥሎም “በምርጫው ሊፈጠር የሚችለውን የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ሁከትና ብጥብጥ ለማስቆም በማደራጀት መረጃ ለመጥለፍ አመችነቱ የላቀ እንደሚሆን ታምኖበታል” በማለት መረጃ መጥለፍ የዩኒቨርስቲዎችና የትምህርት ሚኒስቴር ሥራ እንደሆነ አድርጎ ያቀርባል።
የማንዋሉን ዓላማዎች በሚገልፀው ክፍል ደግም “… የከፍተኛ ትምህርት የትምህርት የልማት ሰራዊት ግንባታን ወይም የፓለቲካ ሰራዊት ግንባታ በሁሉም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በተደራጀና በተናቀጀ ሁኔታ በማቀጣጠልና በማስቀጠል … ምርጫ 2007 ውጤታማ ለማድረግ እና የኢህአዴግን አሸናፊነት ለማረጋገጥ ነው” በማለት ተቋማቱን የኢህአዴግ የምርጫ መሣሪያ መሆናቸውን፤ ግባቸውም የኢህአዴግ አሸናፊነትን ማረጋገጥ መሆኑ ይገልፃል።
በገጽ 3 ላይ ደግሞ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች “በኢህአዴግ ላይ ያላቸው አቋም የወረደ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ በማንኛውም ተቃውሞ ድምፅ ከተጠሩ፤ ሰልፍ የሚያደምቁ፤ ተቃውሞን ከግብ ለማድረስ ሁነኛ መሳሪያ ናቸው። ተማሪዎች በየትኛውም ሐገር እንደታየው አደባባይን የመያዝ ህዝብን አስተባብረው ለተቃውሞ የማሳደም እድላቸው የሰፋ በመሆኑ ከዚህም ሲያልፍ፤ የኢህአዴግ ምከታን በመቃወም ለጠላት ጎራ ተሰልፈው የመታጠቅ እድላቸው ከፍተኛ ነው” ሲል “በወጣቱ እጠላለሁ” የሚለው የህወሓት/ኢህአዴግን ስጋት አፍረጥርጦ ያወጣል። ትንሽ ወረድ ብሎ ደግሞ “በተለይ በአሁኑ ሰዓት ፈተና ላይ የጣለን የምርጫ ጉዳይ እንደምናሸንፍ ቃል የተያዘለት ቢሆንም፤ ፈተናዎች የሚፈጠሩት በህዝብ እና በራሱ ታማኝ ባልሆኑ ሃይሎች ማለትም በመንግስት ክንፍ አይቀለበስም ብሎ ማሰብ አይቻልም። በዚህም ቀድሞ መዘጋጀት ያለበት እና ለሁከት እና ለብጥብጥ መሳሪያ ሊሆን የሚችለው የህዝብ ክንፍ የተማረው ሃይል ሊሆን ስለሚችል ሊታሰብበት ይገባል” ሲል በተማረው ወጣትና የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሠራተኞች ላይ ያለው ጥርጣሬና ፍርሃት ምን ያህል ከፍተኛ እንደሆነ ይገልፃል።
የ2007 ምርጫ በህወሓት ሹማምንት ላይ የፈጠረውን ጭንቀት በዚህ ሰነድ ላይ በገሀድ የሚታይ በመሆኑ እያንዳንዱ ዓረፍተ ነገር በጥንቃቄ ሊነበብና ሊተነተን የሚገባው ነው። ለምሳሌ በገጽ 6 ላይ ስለዩኒቨርስቲ ተማሪ ሲገልጽ “የአመፅ እና የብጥብጥ መነሻ ሊሆን የሚችል ሀይል መሆኑን በአክራሪዎች ሲጠለፍ፤ ከመንግስት ሃይማኖቱን እየመረጠ በባህር ዳር ዩኒቨርስቲ፤ በጅማ ዩኒቨርስቲ፤ በመቀሌ ዩኒቨርስቲ እና በሌሎችም ትምህርቱን ትቶ ሲኮበልል ተመልክተናል” ይላል። ለተማሪዎች፣ ከመንግሥት እና ከሃይማኖት አንዱን እንዲመርጡ ተደርጎ ሃይማኖታቸውን የመረጡ መኖራቸውን እና ይህ ደግሞ አደገኛ ነገር መሆኑን ነው ይህ ዓረፍተ ነገር የሚነግረን። ለመሆኑ ይህ ምን የሚሉት ምርጫ ነው? በእንዴት ያለ ሥርዓት ነው ዜጎች ከመንግስትና ከሃይማኖት አንዱን ምረጡ የሚባለው? እንዲህ ዓይነት ምርጫ ቀርቦ ሃይማኖትን መምረጥ እንዲህ ክፉ ነገር የሆነው ለምንድነው? ይህ ጉዳይ ብቻውን ብዙ የሚያነጋገር ነገር አለው።
በገጽ 8 ላይ ደግሞ “ከፍተኛ አመራሩ ተቋማዊ ለውጥ እንዲሁም የትምህርት ልማት ሰራዊት ግንባታ ቴክኒካዊ ሳይሆን ፓለቲካዊ ጉዳይ መሆኑን ተገንዝቦ ካለእርሱ ባለቤትነትና ቀጥተኛ ተሳትፎ ሰራዊት መገንባት እንደማይቻል በመገንዘብ የመሪነት ሚናውን ካለምንም ማወላዳት መወጣት ይጠበቅበታል” በማለት እየተሠራ ያለው የፓርቲ ወገንተኛ የሆነ ፓለቲካ መሆኑን ብቻ ሳይሆን የትምህርት ተቋማት መሪዎች ዋና ተልዕኮ ትምህርት ማስተማር ሳይሆን የወያኔ ፖለቲካን ማስፈጸም መሆኑን ምንም ሳይጎረብጠው ፍርጥርጡን ያወጣዋል። ትንሽ ወረድ ብሎም “የጋራ መግባባት የምንለካው በመጀመሪያ ለምርጫው የኢህአዴግ የድጋፍ የድል ሰራዊት ብዛት ነው” በማለት ከላይ ያለውን በማጠናከር ወገንተኛነቱም ለኢህአዴግ መሆኑ ያውጃል። በመጨረሻም “ … ሁሉም የዩኒቨርስቲ ፕሬዚዳንቶች ውጤታቸው የሚሞላላቸው ለምርጫው በሚያዘጋጁት የድጋፍ ሃይል ይወሰናል” በማለት የአካዳሚ ነፃነት ብቻ ሳይሆን የከፍተኛ ትምህርት ሥርዓትን ለቀብር ያዘጋጃል።
ይህ ነው የህወሓት የትምህርት ፓሊሲ! የዩኒቨስቲዎች ቁጥር ለማመን በሚቸግር መጠን ቢጨምር፤ የከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎች ቅበላ በብዙ መቶኛዎች ቢያድግ ጥቅሙ ምኑ ላይ ነው። በእንዲህ ዓይነቱ ፓሊሲ ከተገነባ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋም ይገኛል የምንለው ፋይዳ ምንድነው?
ህወሓት በገሀድ በጠላትነት የፈረጃቸው የአገራችን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ መምህራንና ሠራተኞች ይህንን አሳሳቢ ጉዳይ በአጽንኦት እንዲመለከቱ ግንቦት 7፣ የፍትህ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ያሳስባል። ትውልድንም የትምህርት ሥርዓቱንም የማዳን ግንባር ቀደም ኃላፊነት በተማሪዎችና በመምህራን የወደቀ ሸክም ነው ብሎ ግንቦት 7 ያምናል። መላው የትምህርት ሥርዓት ለአንድ ፓርቲ የምርጫ ውድድር መሣሪያነት ሲውል ማየት እና የዩኒቨርስቲ ፕሬዚዳንቶች የሥራ አፈፃፀም የሚወሰነው ለገዢው ፓርቲ ባስገኙት ድምጽ ብዛት ነው መባሉ፤ እነሱም ይኸንን ተቀብለው መሥራት መቀጠላቸውን የመሰለ አሳፋሪ ነገር በአካዳሚያ ውስጥ የለም። የከፍተኛ ትምህርት ተቋሞቻችን ይህን ውርደት መቀበል የለባቸውም። ሰነዱ ህወሓት ከፍተኛ ትምህርትን የሚመለከትበት ዕይታ ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ነውና ለምርጫ ወቅት ብቻ የተዘጋጀ የአጭር ጊዜ መመሪያ ተደርጎ መወሰድ የለበትም። ይህ ሰነድ ህወሓት፣ ተማሪዎችንና መምህራንን እንደጠላት፤ ተቋማቱን ደግሞ ጠላትን እንደመቆጣጠሪያ መሣሪያ እንደሚመለከት፤ ይህ ዕይታው ደግሞ ቋሚ መሆኑ በግልጽ ያሳያል። በህወሓት ዕይታ ከተገነቡ ተቋማት ምን ዓይነት ትምህርት ይገኛል?
የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ መምህራን፣ የትምህርት ኃላፊዎችና ፕሬዚዳንቶች ሆይ! ለገዛ ራሳችሁ ክብር፣ ለአካዳሚ ነፃነት፣ ለትውልድ ስትሉ በዚህ መመሪያ ላይ አምጹ! “እንቢ፣ አሻፈረን፣ በዚህ መመሪያ አንገዛም” በሉ! የኢትዮጵያ ሕዝብ ከጎናችሁ ይቆማል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!

ታሪክን ማደብዝዝም ማጥፋትም አይቻልም!


በአለማችን በተለይ አፍሪካ ዉስጥ የአገርን ብሄራዊ ኃብት የሚዘርፉ፤የህዝብን መብት የሚረግጡና አገርን እነሱ ባሰኛቸዉ አቅጣጫ ብቻ ይዘዉ የሚነጉዱ አያሌ ፈላጭ ቆራጭ መንግስታት አሉ። እነዚህ ህዝብን የሚበድሉ መንግስታት ሁሉም በጥቅሉ አምባገነን ይባሉ እንጂ በመካከላቸዉ ጎላ ብሎ የሚታይ ትልቅ ልዩነት አለ። ሀኖም የቱንም ያክል ልዩነት ቢኖርም እንደ ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች እንመራዋለን የሚሉትን ህዝብ የሚንቁና የኛ ነዉ የሚሉትን አገር የሚጠሉ አምባገነን መንግስታት የሉም፤ በታሪክም ኖረዉ አያዉቁም። አምባገነን መንግስታት የስልጣን ዘመናቸዉን ለማራዘምና ከስልጣን ጋር ተያይዞ የሚመጣዉን ክብር፤ ዝናና ጥቅማ ጥቅም እንዳይቋረጥ ሲሉ የሚቃወማቸዉንና ለስልጣን ዘመናቸዉ አደጋ ነዉ የሚሉትን ሁሉ ያስራሉ፤ ይደበድባሉ ወይም ይገድላሉ። እነዚህን ነገሮች የወያኔ መሪዎችም ያደርጋሉ፤ ነገር ግን በወያኔና በሌሎቹ አምባገነን አገዛዞች መካክል እጅግ በጣም ትልቅ ልዩነት አለ። ለምሳሌ ወያኔዎች ዘረኛ አምባገነኖች ናቸዉ፤ የወያኔ መሪዎች ኢትዮጵያን እንደ ጥገት ላም አንጂ እንደ አገራቸዉ አይመለከቱም። ከዚህ በተጨማሪ ኢትዮጵያን፤ ህዝቧንና ታሪኳን ይንቃሉ፤ ያንኳስሳሉ።
ባለፉት አምስትና ስድስት አመታት በግልጽ እንደተመለከትነዉ የወያኔ መሪዎች የኢትዮጵያን ገበሬ ከመሬቱ አፋናቅለዉ ለምለም መሬቱን ለባዕዳንና ለህወሓት የጦር መኮንኖች ሰጥተዋል። መሬቴንና ቤቴን አልለቅም ብሎ የተቀናቀናቸዉን ደግሞ በጅምላ ገድለዋል። በከተሞች ዉስጥም ከተሜዉን ምንም ካሳ ሳይከፍሉት ዕድሜ ልኩን ከኖረበት ቤቱ እያፈናቀሉ ከነቤተሰቡ ሜዳ ላይ ጥለዉት መሬቱን ባለኃብት ለሚሏቸዉ የወያኔ ባለሟሎች ሰጥተዋል። በአጠቃላይ የወያኔ መሪዎች በኢትዮጵያ አንድነት፤ በታሪኳና በህዝቧ ላይ እንዲህ ነዉ ተብሎ ለመናገር የሚዳግት ትልቅ በደል ፈጽመዋል። ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች በእናት አገራችን ላይ ያደረሱት በደል ተዘርዝሮ የሚያልቅ አይደለምና ዛሬ ወደዚያ ዝርዝር ዉስጥ አንገባም፤ ዛሬ ትኩረት የምንሰጠዉ ወያኔ ደግሞ ደጋግሞ ከዘመተባቸዉና ሙሉ ኃይሉን ካሳረፈባቸዉ የአገራችን እሴቶች አንዱ ታሪካችን ነዉና የዛሬዉ ቆይታችን በዚሁ በታሪካችን አካባቢ ይሆናል።
ታሪክ በአንድ አገር ዉስጥ እያንዳንዱ ትዉልድ ከሱ የቀደመዉ ትዉልድ በግል፤ በቡድንና በማህበረሰብ ደረጃ የተጓዘበትን መንገድ ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ካለፈዉ የምንማርበትና የወደፊቱን ጉዟችንን ለመጀመር በመረጃነት የሚያገለግለንን እዉቀት የምናገኝበት የጥበብ ድርሳን ነዉ። የማንም አገር ታሪክ ዉብ ሆኖ የሚያምርና የማያምር ሁለት ገጽታዎች አሉት፤ የማያምረንን የታሪክ ጠባሳ ወደ ኋላ ሄደን ማከም በፍጹም እንደማንችል ሁሉ የወደፊቱን ታሪካችንንም የብዙ ማህበረሰባዊ መስተጋብሮች ዉጤት ነዉና ያሰኘንን ቅርጽና ይዘት ልንሰጠዉ አንችልም። የታሪክ ዋናዉና ትልቁ ቁም ነገር የታሪኩ ባለቤት የሆነዉ ማህብረሰብ እራሱን ወደ ኋላም ወደ ፊትም የሚመለትበት መስኮት መሆኑ ነዉ። ምንም አይነት ታሪክ የሌለዉ ህብረተሰብ የለም፤ ካለም ከየት አንደመጣና ወዴት አንደሚሄድም አያዉቅም።
አገራችን ኢትዮጵያ ረጂምና ጥንታዊ ታሪክ ካላቸዉ ጥቂት አገሮች ዉስጥ አንዷ ናት። ይህ ረጂም ታሪካችን ደግሞ አንገት ቀና የሚያስደርግ የድልና የገድል ታሪክ አንደሆነ ሁሉ አንገት የሚያስደፋ የግፍና የበደል ታሪክም አለበት። የዛሬዉ ትዉልድ ኢትዮጵያዊ ካለፈዉ ታሪኩ ከበደሉም ከገድሉም ተምሮ የወደፊት አካሄዱን ከሞላጎደል መቆጣጠር የሚችል እድለኛ ትዉልድ ነዉና አባቶቹ ባቆዩለት ታሪክ ሊኮራ ይገባል። አንድ ህዝብ በታሪኩ እንዲኮራ ደግሞ ታሪኩ በተደጋጋሚ ሊነገረዉ ሊተረክለትና በጽሁም መልክትም በገፍ ሊቀርብለት ይገባል። የአገራችን የኢትዮጵያ ህዝብ ግን ለዚህ የታደለ አይደለም ፤ ምክንያቱም እንመራሀለን የሚሉት መሪዎቹ ታሪኩን የሚያንቋሽሹና የሚንቁ መሪዎች ናቸዉ።
ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ካደረሱትና ዛሬም በማድረስ ላይ ካሉት በደሎች አንዱና ዋነኛዉ የኢትዮጳያን ታሪክ ለባዕዳንና የታሪኩ ባለቤት ለሆነዉ የኢትዮጵያ ህዝብ አሳንሰዉና እንደ ተራ ዕቃ አቃልለዉ ማቅረባቸዉ ነዉ። የወያኔ መሪዎች አዲስ አበባን ሲቆጣጠሩ መጀመሪያ ከተናገሯቸዉ ንግግሮች አንዱ የኢትዮጵያን ህዝብ ታሪክ የመቶ አመት ታሪክ ነዉ ያሉት አስቀያሚ ንግግር ነዉ። በዚህ አባባል ላይ የጸና አቋም ካላቸዉ የወያኔ መሪዎች ዉስጥ ዛሬ በህይወት የማይገኘዉ መለስ ዜናዊና ጓደኛዉ ስብሐት ነጋ ዋና ዋናዎቹ ናቸዉ። የሚገርመዉ እነዚህ የኢትዮጵያን ታሪክ በአንድ መቶ አመት የወሰኑት ሁለት ግለሰቦች የተወለዱት የኢትዮጵያ ህዝብ የዛሬ 119 አመት በአፄ ሚኒልክ መሪነት ወራሪዉን የጣሊያን ጦር አይቀጡ ቅጣት በቀጡበት አድዋ ዉስጥ ነዉ።
ወያኔ ካለፈዉ መስከረም ወር ጀምሮ ባደበዘዘዉ ቁጥር እያሸበረቀ ያሰቸገረዉን የኢትዮጵያ ታሪክ ለማቆሸሽ ጠባሳዉ ከትዉልድ ወደ ትዉልድ የሚተላለፍ የክፋት ስራ እየሰራ ነዉ። ኢትዮጵያን የመሰለ ባለታሪክ አገር ገድሎ ለሞተዉ ዘረኛ ሰዉ ትልቅ ማዕከል በህዝብ ገንዘብ የሚያሰሩት የወያኔ መሪዎች ማስቀመጫ ቦታ ጠፋ እያሉ አያሌ ብርቅ የሆኑ የኢትዮጵያ ታሪክ መጽሀፍትን ከወመዘክር አይወጡ በችርቻሮ እየሸጡ ነዉ። እነዚህ ወያኔ የሚሸጣቸዉ መጽሐፍት የተጻፉት በተለያዪ ዘመናት ወደ ኢትዮጵያ መጥተዉ በነበሩት የእንግሊዝ፤ የፈረንሳይ፤ የጣሊያን፤ የስፔንና የጀርመን የታሪክ ጸሐፊዎች ነዉ። ከሰሞኑ ከአዲስ አበባ የሚመጡ ዜናዎች እንደሚያመለክቱት ወያኔ በዉጭ አገር የታሪክ ጸሐፊዎች የተጻፉትን የታሪክ መጽሐፍትና ተጠረዝዉ የተቀመጡ ቆየት ያሉ ጋዜጣዎችን በርካሽ ዋጋ እየቸበቸቡ የግሮሰሪ ዕቃ መጠቅለያ አድርጓቸዋል።
ይህንን አሳፋሪ የሆነ የወያኔ የመጽሐፍ ሽያጭ እንደ ተራ ወንጀል የምናልፍ ኢትዮጵያዉያን ካለን እጅግ በጣም ተሳስተናል። ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች የሚሰሩትን ስራ አበክረዉ የሚያዉቁ ሰዎች ናቸዉ፤ እያሰሩ ያሉት ስራ ደግሞ ግልጽ ነዉ። ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች የተጻፈ ታሪካችንን ብቻ ሳይሆን እያወደሙ ያሉት ባህላችንን፤ ወጋችንንና ቅርሶቻችንን ጨምር ነዉ እንዳልነበረ ያደረጉት። ለምሳሌ በብዙ የአለም አገሮች ዉስጥ ረጂም ዕድሜ ያስቆጠሩ ህንፃዎች፤ የታሪካዊ ሰዎች መኖሪያ ቤቶችና የተለያዪ የአገር ቅርሳቅርሶች ልዩ እንክብካቤ እየተደረገላቸዉ ከዘመን ወደ ዘመን እንዲተላለፉ የደረጋል። ኢትዮጵያ ወስጥ ግን ዕድሜ ለወያኔ ከፍተና ታሪካዊ እሴት ያላቸዉ ህንፃዎች በልማት ስም እንዲፈርሱ ይደረጋል። የጀግኖችን አጽም ያረፈበት የመቃብር ቦታም በግሬደር እየተደረመሰ የንግድና የችርቻሮ ቦታ ይሆናል።
ሌለዉ ወያኔ በታሪካችን ላይ የሚያደርሰዉ ጥፋት ታሪካችንን እንዳንማርና የታሪክ ተማራማሪዎቻችን በጥንታዊ ታሪካችን ላይ ምርምር እንዳያደርጉ እጅና እግራቸዉን ማሰሩ ነዉ። ለምሳሌ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዉስጥ የሚገኛዉ የታሪክ ዲፓርትመንት የኢትዮጵያን ታሪክ ማስተማር ብቻ ሳይሆን ታሪካችንን ከተለያየ አቅጣጫ በማጥናትና ምርምር በማድረግ ለታሪካችን መበልጸግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያደርግ ተቋም ነዉ። ሆኖም ይህ በተለያዪ መንግስታት ዉስጥ ለረጂም አመታት ትልቅ ስራ ሲሰራ የቆየዉ የታሪክ ዲፓርትመንት ዛሬ አለ ተብሎ መናገር በማይቻልበት አሳዛኝ ሁኔታ ላይ ይገኛል። ይህ ሁሉ የሚያሳየን ወያኔ የቀድሞ ታሪካችንን እያወደመ የሚቀጥለዉን ታሪካችንን ደግሞ በራሱ አቅጣጫ እያጣመመ በመጻፍ ላይ መሆኑን ነዉ።
ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች የኢትዮጵያን ታሪክ አስመልክቶ በአንድ በኩል የኢትዮጵያ ታሪክ የተጻፈዉ በተወሰኑ ሰዎች ከአንድ አቅጣጫ ብቻ ነዉ ሲሉ በሌላ በኩል ደግሞ የረጂሙን ዘመን የአገራችን የኢትዮጵያ ታሪክ ከአንድ ሞቶ አመታ የበለጠ ዕድሜ የለዉም እያሉ በተደጋጋሚ ተናግረዋል። ዛሬ በገፍ ለጨረታ ያቀረቧቸዉ የታሪክ መጽሐፍት ቁልጭ አድርገዉ የሚናገሩት ደግሞ ታሪካችን ከ3000 ሺ አመታት በላይ መሆኑንና የተጻፈዉም በተወሰኑ ሰዎች ብቻ ሳይሆን በተለያዪ ኢትዮጵያዉያንና የዉጭ አገር ሰዎች ጭምር መሆኑንደ ነዉ። ዛሬ ወያኔ እንደ ርካሽ ዕቃ እያወጣ የሚቸበችባቸዉ መጽሀፍት ለዚህ አሳዛኝ ዕጣ የበቁት ይህንን የወያኔ አይን ያወጣ ዉሸት ስለሚያጋልጡ ነዉ።
አገራችን ኢትዮጵያን እንወዳለን የምንል ኢትዮጵያዉያን በሙሉ ይህ በአፋችን ሁሌም የምንለዉ ቃል በተግባር የምንተረጉምበት አጋጣሚ ፊት ለፊታችን ላይ ተደቅኗል። ኢትዮጵያ አንደ ገና ዳቦ ከላይና ከታች ወያኔ ባነደደዉ ረመጥ እሳት እየተለበለበች ነዉ። ይህንን እሳት ማጥፍትና አገራችንን ከወያኔ መታደግ ካለብን ግዜዉ ነገ ሳይሆን ዛሬ ነዉ።
አያሌ ኢትዮጵያዉያን የወያኔን የመጽሐፍ ሽያጭ አስመልክቶ የወሰዱትን ቆራጥና ብልህ እርምጃ ግንቦት ሰባት የፍትህ፤ የነጻነትና፤ የዲሞክራሲ ንቅናቄ እጅግ በጣም ያደንቃል። በአዲስ አበባና በአካባቢዋ የሚገኙ አያሌ አገር ወዳድ ኢትዮጵያዉያን የአገርና የወገን ሃላፊነት ተሰምቷቸዉ ወያኔ ለጨረታ ያቀረበዉን መጽሐፍ በመግዛት የአገራቸዉን ታሪክ ለመታደግ ያደረጉት ጥረት በዋጋ ሊተመን የማይችል ትልቅ አገራዊ ስራ ነዉ። አገራችን ዛሬ ባለችበት ሁኔታ ነገ አትገኝም የሚል እምነታችን የጸና ነዉና እነዚህን የገዛችኋቸዉን መጽሀፍት በጥንቃቄ በመያዝ ሀላፊነትና የአገር አደራ ለሚሰማዉ በህዝብ የተመረጠ መንግስት አንድታስረክቡ አደራ እንላችኋለን። ከአሁን በኋላም ቢሆን የወያኔን ፀረ አገርና ፀረ ህዝብ ስራ እየተከታተላችሁ እንድታከሽፉና በሚያልፈዉ ህይወታችሁ የማያልፍ ታሪክ ሰርታችሁ ወያኔን በማሰወገዱ ዘመቻ ዉስጥ ሙሉ ተሳትፎ አንድታደርጉ አገራዊ ጥሪ እናስተላለፋለን።